Friday, August 28, 2015

ኤርትራ ሄደው ግንቦት 7ን ሊቀላቀሉ ነበር ተብለው በተከሰሱት ላይ ምስክርነት ተሰማ

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
የኢትዮ-ኤርትራ ድንበርን አቋርጠው ኤርትራ የሚገኘውን ግንቦት ሰባት የተባለ በተወካዮች ም/ቤት ሽብርተኛ የተባለ ድርጅትን ሊቀላቀሉ ሲሄዱ ተይዘዋል በሚል የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው እነ ብርሃኑ ተ/ያሬድ ላይ የአቃቤ ህግ ምስክር ተሰማ፡፡
ዛሬ ነሀሴ 22/2007 ዓ.ም በፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት የቀረቡት አንደኛ ተከሳሽ ብርሃኑ ተ/ያሬድ፣ ሁለተኛ ተከሳሽ እየሩሳሌም ተስፋው፣ ሦስተኛ ተከሳሽ ፍቅረማርያም አስማማው እንዲሁም አራተኛ ተከሳሽ ደሴ ካህሳይ ‹‹አቃቤ ህግ በጻፈውና ለተከሳሽ በደረሰው የክስ ማመልከቻ ላይ አቃቤ ህግ የሰው ማስረጃ (ምስክር) አልጠቀሰም፤ እኛም መቃወሚያ ስናስገባም ሆነ እምነት ክህደት ቃል ስንሰጥ ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፤ በመሆኑም የአቃቤ ህግ ምስክር ሊሰማብን አይገባም›› በሚል ተቃውሞ ቢያቀርቡም አቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ ባስገባው ክስ ላይ ምስክሩን መጥቀሱን በማስረዳት ምስክሩ እንዲሰሙለት ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ የደረሰው የክስ ማመልከቻ ላይ ምስክር እንደተመዘገበ በማረጋገጥም ብቸኛ ሆነው የቀረቡትን አንድ የአቃቤ ህግ ምስክር ሰምቷል፡፡ ምስክሩም ከ1ኛ፣ 2ኛ እና 3ኛ ተከሰሾች ጋር ሰማያዊ ፓርቲ በሰላማዊ ትግል ውስጥ ሆነው እንደሚተዋወቁ፣ የካቲት 12/2007 ዓ.ም በ1ኛ እና 2ኛ ተከሳሽ አማካኝነት ሰላማዊ ትግሉ እንዳላዋጣ በመጥቀስ ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ መጓዝ ማሰባቸውን ገልጸውለት በዚያው ቀን ማታ 3ኛ ተከሳሽን ጨምሮ ወደ ባህር ዳር እንደተጓዙ ለችሎቱ አስረድቷል፡፡
ባህር ዳር ሲደርሱ ጠዋት ላይ ግን ምስክሩ ሀሳቡን በመቀየር ወደ አዲስ አበባ መመለስ እንደሚፈልግ እንደገለጸላቸው፣ 1ኛ ተከሳሽ በበኩሉ ‹ጎንደር ላይ የምናገኘው ሰው ስላለ ቢያንስ እሱን ካገኘኸው በኋላ መመለስ ትችላለህ› እናዳለው፣ ነገር ግን ምስክሩ በሀሳቡ ባለመስማማት ወደ አዲስ አበባ መመለሱንና ሌሎቹ ሦስቱ ግን ጉዟቸውን መቀጠላቸውን አስረድቷል፡፡ ‹‹ባህር ዳር ላይ ለምን ለመመለስ ወሰንህ›› የሚል መስቀለኛ ጥያቄ ከ1ኛ ተከሳሽ የቀረበለት ምስክሩ፣ ‹‹በወቅቱ ስሜታዊ የሚያደርጉ የግል ጉዳዮች ስለነበሩብኝ በስሜታዊነት የወሰንኩት ውሳኔ በመሆኑ ነው›› ሲል ተናግሯል፡፡
ምስክሩ ‹‹ለምስክርነት ያስገደደህ አካል የለም ወይ›› ተብሎ ሲጠየቅ ‹‹የለም›› የሚል መልስ ሰጥቷል፡፡ ‹‹ግንቦት ሰባት ነጻ አውጭ ድርጅት ነው ወይስ አሸባሪ›› ተብሎ በተከሳሾች መስቀለኛ ጥያቄ ተነስቶ፣ አቃቤ ህግ ተቃውሞውን በማሰማት ‹‹ድርጅቱ በተወካዮች ም/ቤት አሸባሪ ተብሏል፡፡ ይህ የህግ ጉዳይ ነው›› በማለት ጥያቄውን ምስክሩ የመመለስ ግዴታ እንደሌለባቸው አስረድቷል፡፡ ፍርድ ቤቱም ይህን ተቃውሞ ተቀብሎ ምስክሩ ጥያቄውን እንዲያልፉት ተደርጓል፡፡ ‹‹ማዕከላዊ ታስረህ ነበር፣ ድብደባም እንደደረሰብህ በሚዲያ ሳይቀር ተዘግቧል፡፡ ልክ ነው?›› ተብሎ በመስቀለኛ ጥያቄ ሲጠየቅ ምስክሩ ‹‹ማዕከላዊ ቃል እንድሰጥ ተደርጌያለሁ፤ ግን አልታሰርኩም›› የሚል መልስ ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ የምስክሩን ቃል ከሰማ በኋላ የአቃቤ ህግን አስተያየት የጠየቀ ሲሆን፣ አቃቤ ህግ የምስክሩ ቃልና የሰነድ ማስረጃውን መርምሮ ፍርድ ቤቱ ብይን እንዲሰጥለት ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቱም ብይኑን ለማሰማት ለመስከረም 5/2008 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል

No comments:

Post a Comment