Sunday, August 23, 2015

ከ380 በላይ ሰዎች ተይዘው ድብደባ እየተፈጸመባቸው ሲሆን፣ ከዚህ ቁጥር ውስጥ ገሚሶቹ ሴቶች ናቸው::


ኢሳት ዜና :-ሁለት ወጣቶች ጫካ መግባታቸውን ተከትሎ ተጨማሪ አርሶአደሮች እየተያዙ ነው። እስካሁን ባለው መረጃ ከ380 በላይ ሰዎች ተይዘው ድብደባ እየተፈጸመባቸው ሲሆን፣ ከዚህ ቁጥር ውስጥ ገሚሶቹ ሴቶች ናቸው። አብዛኞቹ ሴቶቹ የተያዙት በርካታ አርሶአደሮች አፈሳውን ለማምለጥ ጫካ መግባታቸውን ተከትሎ በባሎቻቸው ቦታ ሲሆን፣ የተወሰኑት ደግሞ ለሽፍቶች ምግብና ውሃ አቀብላችሁዋል ተብለው ነው። በኦሮምያ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞን በወረ ጃርሶ ወረዳ በሚገኙ 8 ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩ አርሶደአሮች የተያዙት ሻሾ አንበሳ እና ዘላለም ጊዲሳ የተባሉ ሁለት ወጣቶች ከመንግስት የሚደርስባቸውን ጥቃት በመሸሽ መሸፈታቸው ተከትሎ ነው። አርሶአደሮቹ ኤጀርሳ ትምህርት ቤት ውስጥ ታስረው ልብሶቻቸውን እንዲያወልቁ እየተደረገ ሌት ተቀን ተደብድበዋል። ቤተሰቦቻቸው ምግብና ውሃ እንዳያቀበሉም ተከልክለዋል። በህጋዊ መንገድ ያስመዘገቡት የግል የጦር መሳሪያ ከየቤታቸው እየተለቀመ ተወስዶባቸዋል። ኢሳት ትናንት ዘገባውን ካቀረበ በሁዋላ፣ ከእስር ቤት በመጥፋት ጫካ ውስጥ የተደበቀ አንድ አርሶ አደር ባስተላለፈው የስልክ መልእክት፣ በኢሳት የቀረበው አሃዝ አነስተኛና ዛሬም ድረስ በርካታ አርሰዶአሮች እየተያዙ ሲሆን፣ በርካቶቹም ጫካ ውስጥ ተደብቀዋል ብሎሏል። ድብደባው ሌት ተቀን እንደሚካሄድና እስካሁን ጫካ የገቡትን ወጣቶች ያሉበትን አካባቢ አውቃለሁ ያለ ሰው አለመኖሩን ገልጿል። አርሶአደሮቹ ከወር በላይ ለሆነ ጊዜ በመታሰራቸው የእርሻ ስራቸውን ለመስራት አልቻሉም። ቤተሰቦቻቸውም በየደረጃው ላሉ ባለስልጣናት አቤት ቢሉም መፍትሄ ሊያገኙ አልቻሉም። መረጃውን ያደረሱን አንድ የአካባቢው ሽማግሌ የኢትዮጵያ ህዝብ መረጃውን ሰምቶ አርሶደሮቹ እንዲለቀቁ ግፊት እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

No comments:

Post a Comment