Monday, August 17, 2015

20 ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ተከሰሱ

ነኅሴ ፲፩ (አስራ አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፍርድ ቤት በቅርቡ ከፍተኛ ቅጣት የጣለባቸው የድምጻችን ይሰማ የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት እንዲፈቱ የጠየቁ 20 ሙስሊም ኢትዮጵያውያን የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸዋል።

ህዝበ ሙስሊሙ በመንግስት ላይ እንዲነሳ ቀስቅሰዋል በሚል በ14ኛ ወንከል ችሎት የተከሰሱት ከድር መሃመድ፣ ነዚፍ ተማም፣ ካሊድ መሃመድ፣ ፉአድ አብዱልቃድር፣ ኢብራሂም ካሚል፣ አብዱ ጁባር፣ ሁሴን አህመድ፣ ሃሚድ ሙሃመድ፣ ቶፊቅ ሚስባህ፣ ዑስማን አብዱ፣ ሙሃመድ ኑሪ፣ አብዱልሃፊዝ ሺፋ፣ ዳርሰማ ሶሪ፣ ፍጹም ቸርነት፣ ሃሮን ሃይረዲን፣ ሸሃቡይን ኑረዲን፣ አያትል ኩበራ፣ ሃሺም አብደላ፣ ሙጂብ አሚኖ እና መሃመድ ከማል መሆናቸውን የስርአቱ ዳጋፊ ሚዲያዎች ዘግበዋል።
ግለሰቦቹ ከአዲስ አበባ፣ ጅማ፣ ወልቂጤ እና ወራቤ ከተሞች መያዛቸው ተዘግቧል። ግለሰቦቹ በተጠቀሱት ከተሞችም የሌሊቱን ክፍለ ጊዜ ተጠቅመው የአመጽ ወረቀቶች መበተናቸው በክሱ ተመልክቷል።
በሌላ በኩል በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች የግድግዳ ላይ ጽሁፎች ተጽፈው አድረዋል።
ባቡር ጣቢያን ጨምሮ በእግረኛ መንገዶች እና በስልክ እንጨቶች ላይም መፈክሮች በብዛት ታይተዋል፡፡ ተጽፈው ካደሩት ከመፈክሮች መካካል የተቀበረች ፍትህ ቀባሪዋን ትቀብራለች፣ ነጻነት እንፈልጋለን፣ በአምባገነኖች ላይ ተነሱ፣ ፍትህ ለታሰሩት፣ አሸባሪው ፍርድ ቤት ፍርድ ቤት ይቀረብ፣ ፍትህ ለሙስሊሞች የሚሉት ይገኙበታል።

No comments:

Post a Comment