Friday, August 14, 2015

የጣልያኑ የመረጃ መረብ ጠላፊ ድርጅት ሃኪን ቲም ከኢትዮጵያ የስለላ ድርጅት ጋር ያለውን ግንኙነት አላቋረጠም ሲል ሂውማን ራይትስ ወች ወቀሰ

ነኅሴ ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ሃኪን ቲም ሰብዓዊ መብትን ከሚያፍኑ መንግስታት ጋር አብሮ መስራቱ ይፋ ከሆነ በሁዋላ፣ ከዚህ ዕኩይ ተግባሩ ይታቀብ ዘንድ በተደጋጋሚ ጊዜ ማሳሰቢያ ቢደርሰውም ፣ አሁንም ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን ግንኙነት አላቋረጠም ሲል ሂውማን ራይትስ ወች በሪፖርቱ ገልጿል።

የጣልያኑ የመረጃ መረብ ጠላፊ ድርጅት ሃኪን ቲም ለተለያዩ መንግስታት የመገናኛ መረብ መጥለፊያ ቴክኖሎጂዎችን በመሸጥና ስልጠና በመስጠት ጭምር አምባገነን መንግስታት ሰብአዊ መብቶችን እንዲጥሱ እገዛ ያደርጋል።
ሀኪንግ ቲም ለኢትዮጵያ የስለላ መረብ ወይም ኢንሳ በሸጠው ሶፍት ዌር፣ ከ 1 ሚልዮን ዶላር በላይ ክፍያ እንዳገኘ ሪፖርቱ ጠቁሟል።ሪፖርቱ ፣ በተለይ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለው ግንኙነት እንዳልተቋረጠና ከኢትዮጵያ የመረጃ መረብ ጠላፊ ድርጅት ኢንሳ ጋር በመተባበር ልዩ ስልጠናዎችን እየሰጠ መሆኑን ገልፆ፣ በቀዳሚነት ጋዜጠኞች፣የሰብዓዊ መብት ተሟጓቾች፣የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት የጥቃቱ ሰለባ ናቸው ብሎአል። የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን ኢሳት፣ የጥቃቱ ዋና ሰላባ መሆኑ ተገልጿል።
ከሃኪን ቲም ጋር የጣሊያን መንግስት ባለስልጣናትም በተዘዋዋሪ እጃቸው እንዳለበት ሪፖርቱ ገልፆ ፣ እንደዚህ ዓይነት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ሲፈፀሙ የጣሊያን መንግስት ችላ ብሎ እንዲያልፈው ሽፋን ይሰጣሉ ብሎአል።

ሃኪም ቲም ባወጣው መግለጫ ከኢትዮጵያ የስለላ ድርጅት ጋር ያለውን ግንኙነት ካቋረጠ አመት እንዳለፈው ገልጿል። ድርጅቱ ግንኙነቱን ያቋረጠው፣ የኢትዮጵያ የስለላ ድርጅት ሰራተኞች ቴክኖሎጂውን በአግባቡ ለመጠቀም ችሎታ የላቸውም በሚል ነው። የኢትዮጵያ መንግስት ተወካይ ስለላውን ያካሄድነው በጋዜጠኛ ላይ ሳይሆን፣ መንግስትን ለመገልበጥ በሚንቀሳቀስ ግለሰብ ላይ ነው የሚል መልስ መስጠቱን የገለጸው ሃኪንግ ቲም፣ ያም ሆነ የስለላ ድርጅቱ ብቃት ስለሌለው ኮንትራቱን ሙሉ በሙሉ ለማቋረጥ ወስነናል ብሎአል። ከአለፈው አንድ አመት ጀምሮ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የለንም ሲል ሃኪንግ ቲም አክሎ ገልጿል።

No comments:

Post a Comment