Tuesday, November 17, 2015

የዓለም የጤና ድርጅት ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የጤና ቀውሶች ተጋላጭ ትሆናለች በማለት አስጠነቀቀ

ኀዳር ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በዓለም ባለው የአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ በኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠነ ሰፊ የሆኑ የጤና ችግሮች እንደሚከሰቱ የዓለም የጤና ድርጅት የአየር ንብረትና የጤና እክሎችን በሚተነትነው ሪፖርቱ አስጠንቅቋል።

በሙቀት መጨመር ሳቢያ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ማዕበል፣ጎርፍና የመሬት መንሸራተት፣ ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብን ተከትሎ በሚፈጠሩ በሽታዎች ሳቢያ የምግብ እጥረትና የጤና መቃወሶች እንደሚያጋጥሙና አስቀድሞ አደጋዎችን ለመከላከል ካልተሞከረ የችግሩ ተጋላጮች ቁጥር እንደሚጨምር ድርጅቱ ስጋቱን ገልጿል።
ኢትዮጵያ በአየር ንብረት መዛባት ሳቢያ ቀዳሚዋ ተጠቂ አገር እንደምትሆንና በወንዞች መሙላት ሳቢያ በሚከሰት ጎርፍ ብቻ በየዓመቱ ከ250 ሽህ በላይ ዜጎች ለችግር ተጋላጭ እንደሚሆኑ አትቷል።
በተጨማሪም የዓለም የጤና ድርጅት ዶ/ር ማርጋሬት ቻን ዓለማችን የሰዎችን ሕይወት በተሟላ ሁኔታ ለመጠበቅ የሚያስችል አቅሟን እያጣች ነው፤ ጠንካራና ተለዋጭ የሆኑ የጤና አጠባበቅ መርሃግብሮችን መንደፍ ያስፈልጋል ሲሉ ጠቁመዋል።

No comments:

Post a Comment