Wednesday, November 18, 2015

ሰማያዊ ፓርቲ ያቀደውን ህዝባዊ ስብሰባ ወደ ሰላማዊ ሰልፍ ለመቀየር መገደዱን ገለፀ

• ‹‹ከደህንነትና ፖሊሶች ጋር ካልተነጋገርኩ አልፈቅድም›› አስተዳደሩ
• ‹‹ሰላማዊ ሰልፍ ለመጥራት እነሱን መለማመጥ አያስፈልግም›› ኢ/ር ይልቃል ጌትነት
ከአባላቱና ደጋፊዎቹ ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ጋር ለመነጋገር ህዳር 18/2008 ዓ.ም ህዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ አቅዶ የነበረው ሰማያዊ ፓርቲ የአዲስ አበባ አስተዳደር በፈጠረበት መሰናክል ምክንያት ያቀደውን ህዝባዊ ስብሰባ ወደ ሰላማዊ ሰልፍ ለመቀየር መገደዱን ሊቀመንበሩ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ባስገባው የእውቅና ደብዳቤ ላይ ‹‹ህዳር 18 አልፏል፡፡ ይቀመጥ!›› ብሎ መርቶበት የነበረው አስተዳደሩ ፓርቲው ‹‹ህዳር 18 አላለፈም›› ባለው መሰረት ‹‹በስህተት ነው፡፡ ሰኞ ኑ!›› ብሎ ሰኞ ህዳር 6/2008 ዓ.ም ተቀጥረው እንደነበር እና ወደ ስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል መመራቱን ተገልጾላቸው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ሰኞ ሲሄዱ ‹‹ዛሬ አይመችም፣ ነገ ኑ›› ተብሎ ለረቡዕ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ዛሬ ህዳር 8/2008 ዓ.ም በቀጠሯቸው መሰረት ከህዳር 6 ጀምሮ ለ3ኛ ጊዜ፤ እውቅናውን ከጠየቀ በኋላ በአጠቃላይ ደግሞ ለ8ኛ ጊዜ ሲሄዱ የስብሰባና ሰላማዊ ሰልፍ ማሳወቂያ ክፍል ‹‹ከደህነትና ፖሊስ ጋር እየተማከርኩ ነው፡፡ ከእነሱ ጋር ሳልማከር አልፈቅድም›› ብሎ እንደመለሳቸው ገልጸዋል፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ ለአስተዳደሩ ደብዳቤ መፃፍ ከጀመረ 15 ቀናት ያለፉት ሲሆን ለ6ኛ ጊዜ ደብዳቤውን ማስገባቱ ይታወቃል፡፡ አስተዳደሩ የሰላማዊ ሰልፍ ወይም የስብሰባ እውቅናን መከልከል እንደማይችል፣ ነገር ግን የደህንነት አሊያም የቦታ ችግር ካለ ቦታ ወይንም ጊዜ ሊቀይር ብቻ እንደሚችል የገለፁት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት በተደጋጋሚ ለአስተዳደሩ ደብዳቤ ለማስገባት የተገደዱት የአዳራሽ ኪራይ ለመክፈል አስደዳደሩ እውቅና ስለሚያስፈልግ መሆኑን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡
ይሁንና ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ለአስተዳደሩ አሳውቆ በ48 ሰዓት ውስጥ መልስ ካልሰጠ እውቅና እንደሰጠ ስለሚቆጠርና የአስተዳደሩን መሰናክልም ስለሚቀንሰው ስብሰባውን ወደ ሰላማዊ ሰልፍ ለመቀየር እየተገደዱ መሆኑን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል ‹‹መስተዳደሩ እንዲህ የሚጠመው የስብሰባ አዳራሽ እንዳናገኝ ነው፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ከሆነ ግን እነሱን ይህን ያህል መለማመጥ አያስፈልግም፡፡ በመሆኑም እንደተለመደው የወሰዱትን እርምጃ ቢወስዱም ስብሰባውን ወደ ሰላማዊ ሰልፍ ለመቀየር እየተገደድን ነው›› ብለዋል፡፡

No comments:

Post a Comment