Thursday, November 12, 2015

የመከላከያ ሰራዊት አባላትን ጭኖ ሲጓዝ የነበረ ኦራል መኪና ተገልብጦ በትንሹ 20 ወታደሮች ህይወታቸው ሲያልፍ በርካቶችም ቆስለዋል

ኀዳር ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ዛሬ ህዳር 2፣ 2008 ዓም ከጎንደር ወደ መተማ ሲጓዙ ከነበሩ ኦራል መኪኖች መካከል አንደኛው ግንድ መጣያ ቀበሌ ልዩ ስሙ ባለእግዚብሄር ቦታ ላይ ሲደርስ ባጋጠመው የቴክኒክ መበላሸት የተነሳ በመገልበጡ በሸራ ተሸፍነው ሲጓዝ ከነበሩት ወታደሮች መካካል 20 የሚሆኑት ወዲያውኑ ሲሞቱ፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው ወታደሮች ቆስለው ወደ ጎንደር ሆስታል ተወስደዋል።

ቦታው ላይ የነበሩ የአይን እማኞች እንደገለጹት፣ ተከታትለው ሲጓዙ ከነበሩት ወታደራዊ ተሽከርካሪዎች መካከል ፊት ላይ የነበረው ተሽከርካሪ ችግር ሲያጋጥመው ወደ ጎን በመገልበጡ፣ በአንድ በኩል ያሉት ሙሉ በሙሉ ሲያልቁ፣ ከሁዋላ የነበሩት አንዳንዶች ዘለው ማምለጣቸውን ሌሎች ደግሞ ክፉኛ ቆሰለው ወዲያውኑ በሌሎች ወታደሮች ሆስፒታል እንዲወሰዱ ተደርጓል። ከተገለበጠው መኪና ሁዋላ ይጓዝ የነበረው ወታደራዊ ተሽከርከሪ የተገለበጠውን መኪና ከሁዋላ በኩል መምታቱንም የአይን እማኞች ተናግረዋል። ወታደሮቹ የፈሰሰውን ደም ሲያጸዱ ማርፈዳቸውን የአይን እማኞች አክለው ገልጸዋል።
ሰሞኑን በሰሜን ጎንደር ዞን የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ በርካታ ቁጥር ያለው የመከላከያ ሰራዊት ወደ አካባቢው ተሰማርቷል። ምንም እንኳ በህዝቡና በልዩ ሃይል አባላት መካከል ሲካሄድ የቆየው ግጭት ጋብ ያለ ቢመስልም አሁንም ውጥረቱ እንዳለ የአይን እማኞች ተናግረዋል።

No comments:

Post a Comment