Thursday, November 12, 2015

በኮንሶ ውጥረቱ ተባብሶ ብዙዎች በጅምላ እየታሰሩ ነው

ኀዳር ፪ (ሁለት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በደቡብ ክልል ሰገን ዞን ኮንሶ ወረዳ የሚገኙ ነዋሪዎች በዞን ደረጃ ራሳቸውን ለማስተዳደር እንዲፈቅድላቸው ጥያቄ በማቅረባቸው ብቻ የብሔረሰቡን አባላት ማሳደድ፣ ማሰር፣ መደብደብ ዘመቻው የቀጠለ ሲሆን፣በአካባቢው ያለው ውጥረት ተባብሷል፡፡

የደቡብ ክልል መንግስት የኮንሶን ጥያቄ በአግባቡ ከመመለስ ይልቅ ጥያቄውን በኃይል ወደማፈን በመሸጋገሩ ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ ከጉዳዩ ጋር እጃቸው አለበት የተባሉ በርካታ ሰዎች ከያሉበት ተለቅመው በአርባምንጭ ከተማ እንዲታሰሩ ተደርጎአል፡፡ ጉዳዩን ተከታትለው እንዲያስፈጽሙ ሕዝብ ውክልና የሰጣቸው የኮሚቴ አባላትም እስርና ድብደባ እየደረሳቸው መሆኑ ታውቆአል፡፡
በተለይ የኮንሶ የሀገር ሽማግሌዎች ባለፈው ሰኞ ወደ አዲስአበባ በመሄድ ለደኢህዴን ሊቀመንበር ለሆኑት ለጠ/ሚ ሃይለማርያም ደሳለኝ የአቤቱታ ደብዳቤ ያቀረቡ ሲሆን፣ ሽምግሌዎቹ በዚሁ ደብዳቤቸው የኮንሶ ሕዝብ በሰላማዊ መንገድ ያቀረበው ጥያቄ እየተሰጠው ያለው ሕገወጥ የሃይል ምላሽ የተነሳ ሕዝብ ወደአልተፈለገ ግጭት ውስጥ እንዳይገባ በፓርቲያቸውም፣ በመንግስታቸውም ባላቸው ሃላፊነት ችግሩን እንዲያስወግዱና የህዝቡን ጥያቄ እንዲመልሱ ጥያቄ ማቅረባቸው የክልሉን ባለስልጣናት አበሳጭቶአል፡፡
በተጨማሪም የኮንሶ ሕዝብ የራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ ሲቀርብ የአካባቢው ተወላጆች የሆኑና በስልጣን ላይ የሚገኙ አንዳንድ የደኢህዴን አባላት ከሕዝቡ በተቃራኒ መሰለፋቸውን በመቃወም በተለይ የሕዝብ ተመራጮችን ውክልናቸውን ለማንሳት ፒቲሽን ተፈራርሞ ለምርጫ ቦርድና ለሚመለከታቸው አካላት ማስገባታቸው በክልሉ ባለስልጣናት ባለመወደዱ ጭካኔ የተሞላበት ኢ-ሰብኣዊ ምላሽ ወደመስጠት እንዳሸጋገራቸው ታዛቢዎች ይናገራሉ፡፡
ኮንሶ አካባቢ በአሁኑ ወቅት በልዩ ሃይል ወታደሮች ከበባ ስር የሚገኝ ሲሆን፣ በመንገድ ላይ የሚገኙ ሰዎች ጭምር ድብደባ ፣ማስፈራራትና ሕገወጥ እስር እየደረሰባቸው መሆኑ ታውቆአል፡፡ በዚህ ምክንያት መንግስታዊ ተቋማትና ት/ቤቶች መደበኛ ስራቸውን ለማከናወን ተቸግረዋል፡፡
ልዩ ሃይሉ ሕዝብ በነቂስ ወጥቶ« እኛ የዞን ጥያቄ አላቀረብንም፣ ጥያቄው የጥቂት ግለሰቦች ነው» በሚል እንዲያወግዙ ያደረጉት ተደጋጋሚ ሙከራ መክሸፉም ውጥረቱን አባብሶታል፡፡
ለደቡብ ክልል ብሄር ብሄረሰቦች ም/ቤት ቅርበት ያላቸው አንድ ባለሙያ በሰጡት አስተያየት የኮንሶ ሕዝብ ጥያቄ ተገቢነት ያለውና የኮንሶ ተወላጅ በሆኑ አንዳንድ የኢህአዴግ ሹማምንት ጭምር ድጋፍ ያለው ቢሆንም ይህ ጥያቄ መመለሱ በክልሉ ለሚገኙ ከ55 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች ተመሳሳይ ጥያቄ እንዲያነሱ መንገድ መክፈት በመሆኑ ምክንያት ክልሉ ጥያቄውን ከኮንሶ ሕዝብ ጋር መክሮና አሳምኖ ሃሳባቸውን ማስቀየር፣ ይህ ካልተቻለ ደግሞ በሃይል ከመጨፍለቅ የተሻለ አማራጭ የለውም ብለዋል፡፡ ነገርግን ከሕዝብ ጋር ሳይማከሩ በማንአለብኝነት ወደሃይል አማራጭ መገባቱ በአካባበቢው መፍትሔ ያመጣል ብለው እንደማያምኑ ተናግረዋል፡፡
በተለይ ጠ/ሚኒስትሩ በሊቀመንበርነት የሚመሩት ፓርቲ እንዲህ ዓይነት አነስተኛ የሕዝብ ጥያቄ እንኩዋን ሰላማዊ በሆነና በሰለጠነ መንገድ መመለስ አለመቻሉ ትልቅ የሕዝባዊ ውግን እና የአመራር ብቃት ላይ ጥያቄን የሚያስነሳ ነውም ሲሉ አክለዋል፡፡
በሰገን ዞን በአሁኑ ወቅት ኮንሶን ጨምሮ 8 ብሄረሰቦች የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህ መካከል ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር የያዘው የኮንሶ ህዝብ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment