Wednesday, November 25, 2015

ገሃዱ አሰቃቂ ረሃብ እና የማወናበጃው «የልማት ዕድገት» በኢትዮጵያ | ሞረሽ ወገኔ

በያዝነው ዓመት በአገራችን በኢትዮጵያ አስከፊ የርሃብ አደጋ እንደተስፋፋ ከተለያዩ የዜና አውታሮች ይደመጣል። በተቃራኒው ደግሞ የትግሬ-ወያኔ የሚቆጣጠራቸው የመገናኛ ብዙሃን በአገዛዙ ጥረት ስለተገኘው የልማት ትሩፋት ይለፍፋሉ። በአንድ አገር በአንድ ጊዜ ሁለት እጅግ ተቃራኒ ሁኔታን የሚያንጸባርቁ ዜናዎች ሲደመጡ እውነቱን አንጥሮ ማሣዬት ተገቢ ነው። ስለሆነም በዚህ መግለጫ ዕውነቱ የትኛው እንደሆነ ብቻ ሣይሆን የመፍትሔ ኃሣቦችንም ለማመልከት ተሞክሯል።  በአገራችን በኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ጊዜያት ከፍተኛ የርሃብ አደጋዎች ተከስተዋል። በዚሁ ሳቢያ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን አልቀዋል፤ አሁንም እያለቁ ነው። ለአብነት ያህል በንጉሡ ዘመን በ1958ዓ.ም. እና በ1965-66 ዓ.ም. እንዲሁም በደርግ ጊዜ በ1977 ዓ.ም. የተከሰቱት የርሃብ አደጋዎች በአስከፊነታቸው እና በሕዝብ ጨራሽነታቸው የሚጠቀሱ ናቸው። በትግሬ-ወያኔ የአገዛዝ ዘመን ርሃብ አልፎ አልፎ የሚመጣ ሣይሆን በየዓመቱ ከ7 እስከ 25 ሚሊዮን የሚደርሱ ኢትዮጵያውያንን ለችጋር ማጋለጡ እና የሰው እጅ ተመልካች እንዳደረጋቸው ይታወቃል። ይህም ሆኖ እንደ ዘንድሮው እጅግ የከፋ አልነበረም። በመሆኑም በዚህ ዘመን ርሃብ በኢትዮጵያውያን ላይ ቤቱን ሠርቷል ለማለት ያስደፍራል። ስለሆነም ሦሥቱም ተከታታይ አገዛዞች አንዱ ካለፈው ገዢ
ስህተት ሊማር ባለመቻሉ ችግሩ እየተባባሰ እንጂ እየቀነሰ አልመጣም።  በሦሥቱም የአገዛዝ ዘመኖች ለርሃቡ መንስኤ ተደርጎ የሚቀርበው ድርቅ ነው። ከፍተኛ የዝናብ እጥረት ሲከሰት ድርቅ ይፈጠራል። ስለዚህ ድርቅ የተፈጥሮ ክስተት በመሆኑ ምንጊዜም የአየር ንብረት አካል ነው። ሆኖም ግን ኢትዮጵያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ወንዞች እና ሐይቆች ያሏት፣ በተፈጥሮ ኃብት የታደለች አገር ናት። ስለሆነም ሕዝብን የሚወክል እና ሕዝባዊ ተሳትፎ ያለው ሥርዓት ካለ፤ የድርቁን ተፅዕኖ ለመቋቋም ይቻላል። ይኽውም፥ ወንዞችን በመገደብ እና የሐይቆችን ውኃ በመጠቀም ከፍተኛ የመስኖ እርሻ ማስፋፋት ይቻላል። እንደሚታወቀው ከ85% የማያነሰው የአገራችን ሕዝብ ከእጅ-ወደ-አፍ በሆነ የግብርና ኢኮኖሚ ዘርፍ የተሰማራ ነው። ይኽ የአገራችን ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት የሆነው ዘርፍ እስካሁን ድረስ የሚዘወረው ከጥንት ጀምሮ ባልተቀየረ ኋላቀር የበሬ እርሻ ነው። «ይህ ኋላቀር የእርሻ ዘይቤ ሣይቀየር አገሪቱ እንዴት በልማት ትሩፋት ልተምነሸነሽ ትችላለች?» ብሎ መጠየቅ ተገቢ ይሆናል። አሁን በአስከፊ ሁኔታ የተከሰተው ርሃብ በሥልጣን ላይ ያለው ፀረ-ሕዝቡ እና ፋሽስቱ የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ የፈጠረው ነው። እንዴትስ ፈጠረው? ምክንያቶቹ፥ ·         የኢትዮጵያ መሬት ብቸኛ ባለቤት የሆነው የትግሬ-ወያኔ ገዥ ኃይል ገበሬውን እጅግ አነስተኛ በሆነ የእርሻ መሬት ስለወሰነው፣ ገበሬው በቂ ምርት ማምረት አልቻለም። ·         ገበሬው የተበላሸ እና ጊዜው ያለፈበት ማዳበሪያ በግድ እንዲገዛ በመደረጉ መሬቱ ተጎድቷል፣ ለምነቱም ቀንሷል። ·         ገበሬው በቀላሉ ገንዘብ የሚገኝበት ሰብል (cash crop)፥ እንደ ጫት፣ አበባ ወዘተርፈ …. እንዲያመርት በሥርዓቱ በመገፋፋቱ የምግብ እህል ምርት አሽቆልቁሏል። ·         በወያኔ የዘር ማጽዳት ፖሊሲ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ገበሬዎች፣ በተለይም ዐማሮች፣ ከነቤተሰቦቻቸው ከቀያቸው በመፈናቀላቸው ምክንያት አምራቾች ሣይሆኑ የዕለት ምግብ የሚመፀወቱ ምንዱባን ሆነዋል። ·         በፍጥነት እያደገ የመጣው የሕዝብ ብዛት የእርሻ መሬት ጥበት በማስከተሉ፣ ሥራ ለመፈለግ ከገጠር ወደ ከተማ የሚፈልሰውን ገበሬ ቁጥር እንዲያሻቅብ አድርጎታል። ይህም በእርሻው ኢኮኖሚ ዘርፍ ላይ ከፍተኛ ውድቀት አስከትሏል። ·         የትግሬ-ወያኔ ሆን ብሎ ከፍተኛ የደን ክምችት ያላቸውን ቦታዎች በየጊዜው በእሳት በማጋየቱ ምክንያት የአገራችንን የተፈጥሮ ሚዛን እና የአካባቢ አየር ንብረት በማዛነፉ ድርቅ በተደጋጋሚ እንዲከሰት አድርጓል። ·         የትግሬ-ወያኔ ከፍተኛ ለምነት ያላቸውን የእርሻ መሬቶች እስከ መቶ ዓመት በሚደርስ የጊዜ ገደብ በሊዝ መልክ ቸብችቧል። መሬት በሊዝ የሚገዙት ራሱ የፈጠራቸው የአገር ውስጥ ከበርቴዎች እንዲሁምየውጭ አገር ከበርቴ ግለሰቦች እና ኩባንያዎች ናቸው። እነዚህም ከበርቴዎች እና ኩባንያዎች የሚያመርቷቸውን ምርቶች የሚያቀርቡት ለአገር ውስጥ ፍጆታ ሳይሆን በቀጥታ ለውጭ አገሮች ገበያ እና ሸማች ይልካሉ።ስለሆነም ኢትዮጵያውያን በእጅ-አዙር ቅኝ አገዛዝ ሥር ወድቀው የበይ ተመልካቾች በመሆናቸው እና በአገራቸው ውስጥ የሥራ እድል ሊያገኙ ስለአልቻሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ወጣት አምራች ኃይሎች ለሥራ እድል ፍለጋ ወደ አረብ አገሮች ለመሰደድ ተገድደዋል። ·         ለተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተብሎ በእርዳታ እና በብድር መልክ ከውጭ የሚገባው ብዙ ቢሊዮን ዶላር፤ እንዲሁም የአገራችን አንጡራ ኃብት በትግሬ-ወያኔዎች ያለማቋረጥ ይዘረፋል። ይህም ድህነት እንዲሠራፋ አድርጓል። ·         የድርቅን አደጋ ተቋቁሞ ርሃብን በዘላቂነት ለመግታት ሠፋፊ የመሠረተ-ልማት ግንባታዎች ማከናወን ወሣኝ ነው። ሆኖም ባለፉ አገዛዞች ከነበረው አዝጋሚ የመሠረተ-ልማት ግንባታ በከፋ ሁኔታ በዘረኝነት መንፈስ የትግራይ ክልል የተባለው ብቻ ተጠቃሚ እንዲሆን ይደረጋል። ከዚህ በተጨማሪም የአገዛዙ ሥርዓት ዕድሜውን ለማራዘም ከአገሪቱ በጀት ከግማሽ የማያንሰውን ለስለላ ሥራ ያውላል። ስለዚህ በርሃብ ወቅት ሕዝቡን ከአደጋ ለመታደግ የሚያስችሉ ከፍተኛ የእህል ጎተራዎች አልተሠሩም፤ ጤና ለመጠበቅ የሚያስችሉ ተቋሞች አልተገነቡም፣ እንዲሁም ወደ ገጠሩ እንደልብ ለመግባት የሚያስችሉ የገጠር መንገዶች አልተዘረጉም። ·         የትግሬ-ወያኔ በሚከተለው የከፋፍለህ-ግዛው ፖሊሲ ምክንያት ሕዝባችንን በዘር፣ በጎሣ እና በኃይማኖት እየለያየ ያጫርሳል።  የእርስ በርስ ግጭቶች እና ጦርነቶች  በተለያዩ አካባቢዎች በመከሰት ላይ ናቸው። ለአብነት ያህል፥ በጎንደር፣ በወሎ፣ በሸዋ፣ በጎጃም፣ በአርሲ፣ በወለጋ፣ በባሌ፣ በኦጋዴን፣ በጋምቤላ፣ በሲዳሞ፣ በጋሙ-ጎፋ፣ በከፋ፣ ወዘተርፈ …. በተደጋጋሚ ጊዜያት ሕዝብ እርስ በእርሱ እንዲጫረስ ተደርጓል። ይህም የአምራቹን ኃይል ቁጥር የሚያመናምን፣ በተቃራኒው ለርሃብ አደጋ የሚጋለጠውን ዜጋ የሚያበዛ ነው። ርሃብ እና ችጋር እንደ ደራሽ ጎርፍ በድንገት አይመጡም። በመጀመሪያ ድርቅ ሲከሰት ሰብሎች ይጠወልጋሉ፣ ምርትም አይገኝም፤ ይህ በትንሹ ከሦሥት ወራት ያላነሰ ጊዜ ይወስዳል። በድርቅ ጊዜ ከብቶች በግጦሽ ሣር እና በውኃ እጦት ይኮሰምናሉ፣ ከዚያም በገፍ ያልቃሉ። ይህ ሁሉ በአንድ ቀን ጊዜ አይከሰትም። ስለዚህ ከድርቅ ጋር የተያያዘን ችጋር ለመቋቋም በአንድ አገር የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ እና የዝግጁነት ሥርዓት ካለ ሕዝብ ለርሃብ አይጋለጥም። ይህ ተሞክሮ ረሃብን ታሪክ ለማድረግ በበቁ አገሮች በተግባር ታይቷል። በእኛም አገር ለአጭር ጊዜም ቢሆን ምልክቱ ታይቶ ነበር። በትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ግን የሚደረገው ሆን ተብሎ የዚህ ተቃራኒ ነው። በአፄ ኃይለሥላሤ ዘመን «የድርቅ ኮሚሽን» በመባል የተቋቋመው መሥሪያቤት በደርግ ዘመን እጅግ ጎልብቶ የአገሪቱን ሕዝብ ከከፍተኛ የርሃብ መቅሰፍት ለመታደግ የሚያስችል ተቋም ለመሆን በቅቶ ነበር። በተደጋጋሚ በርሃብ ሲጠቁ የነበሩ ዜጎችን ለም እና ለኑሮ ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት ባላቸው አካባቢዎች በማስፈር ከተረጂነት ወደተትረፈረፈ ምርት አምራችነት ለመቀየር ተችሎ ነበር። ዛሬ ግን በኢትዮጵያ ውስጥ ከገጠር እስከ ከተማ፣ በሁሉም ሥፍራ የዕርዳታ እህል የማይሠፈርለት ዜጋ በቁጥር ነው። ያም ቢሆን ውጭ አገር ያሉ ዘመዶቹ ገንዘብ የሚልኩለት፤ አልያም የወያኔ ሹመኛ ከሆነ ብቻ ነው። በተለይ ደግሞ ዐማራውን ለይተው ከሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች በዘር ማጽዳት ዘመቻ በማፈናቀል በርሃብ እና በችጋር ይፈጁታል። «ለወያኔ አገዛዝ አንንበረከክም» ያሉትን አፋሮችን እና ሶማሌዎችን በርሃብ ይቆላሉ። በአጠቃላይ ለርሃብ እና ለችጋር የሚያጋልጠው ብልሹ እና ኃላፊነት የጎደላቸው አገዛዞች የሚፈጥሩት ችግር እንጂ ድርቅ ብቻውን ሊሆን አይችልም። ድርቅ ብቻውን ርሃብ የሚያመጣ ቢሆን ኖሮ የዝናብ ጠብታ የማያውቁ አገሮች ዜጎች ገና ጥንት ከምድረ-ገፅ ይጠፉ ነበር። አንዳንድ ጸሐፊዎች «ፖለቲካ እና ሰብዓዊነት መያያዝ የለበትም» የሚለውን ኃይለ-ቃል ደጋግመው ይናገራሉ። ሆኖም ይህን የሚናገሩት በአፄ ኃይለሥላሤም ሆነ በደርግ የአገዛዝ ዘመኖች ለተከሰቱት የርሃብ ችግሮች ምንጮቹ የአገዛዝ ሥርዓቶቹ መሆናቸውን ሲያስተጋቡ የኖሩት ናቸው። ዛሬ ታዲያ ካለፉት ሁለት የአገዛዝ ሥርዓቶች እጅግ በከፋ ሁኔታ ኢትዮጵያውያንን ለማያባራ የርሃብ ችግር የዳረጋቸው የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ሆኖ ሳለ ከዚህ ፍርድ እንዴት ሊያመልጥ ይችላል? የትግሬ-ወያኔዎች ኢትዮጵያውያንን በርሃብ እያቆራመዱ ዶላር ለመሰብሰብ የበሰለ ምግብ ወደ ውጪ አገሮች ይልካሉ። በአገር ቤት ግን ዜጎች የሚጣል የምግብ ትርፍራፊ በጉርሻ መልክ እየገዙ ሕይዎታቸውን ለማቆየት ይፍገመገማሉ። በየዓመቱ በርሃብተኛው ስም በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር ገንዘብ በዕርዳታ መልክ ከውጪ የሚለገሣቸው ወያኔዎች ገንዘቡን ወደ ውጪ አገሮች መልሰው እያሸሹ እነርሱ ቢሊዬኔሮች ሆነዋል፤ አሁንም ግን በርሃብተኛው ስም ከውጪ ዕርዳታ ይለመናል። ስለዚህ ኢትዮጵያውያን በማንኛውም የአገር ውስጥም ሆነ ዓለም-አቀፍ ድርጅት አማካይነት በርሃብተኞች ስም የሚደረገውን ዕርዳታ ፋይዳው ምን እንደሆነ ቆም ብለን ልናስብብት ይገባናል። ለወገን ደራሹ ወገን ነውና ለርሃብተኛ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ካለማንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ የዕርዳታ እጃችንን እንዘርጋላቸው። ሞረሽ-ወገኔም ለዚህ የተቀደሰ ተግባር አስፈላጊውን መሠናዶ ያደረገ ስለሆነ ዕርዳታችሁን በተገቢው ሁኔታ ለማድረስ ዝግጁዎች ነን፤ በአድራሻችን ጠይቁን። ሆኖም ምንጊዜም ማስታወስ ያለብን ዘለቄታዊ መፍትሔ የሚመጣበትን መንገድ ነው። የትግሬ-ወያኔ ካለ፣ ርሃብ እና ችጋር ይቀጥላል። ስለሆነም ለዚህ ዓይነቱ ሁኔታ የዳረገን የችግራችን ሁሉ ምንጭ የሆነው የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ መወገድ አለበት። ስለዚህ ኢትዮጵያውያን ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ በአንድነት ተንቀሳቅሰን የችግሮቻችን ሁሉ ምንጭ የሆነውን የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ለማስወገድ ቆርጠን እንነሣ። ርሃብን ታሪክ ለማድረግ ቆርጠን እንነሣ! የትግሬ-ወያኔን አገዛዝ በተባበረ ክንድ እናስወግድ! - 

No comments:

Post a Comment