Wednesday, November 25, 2015

በምዕራብ ወለጋ መንዲ ከተማ አደባባይ የወጣ ከፍተኛ ተቃውሞ ሲሰማ ዋለ * ህዝቡ ጎማ እያቃጠለ ነበር

(ዘ-ሐበሻ) በምእራብ እና በመካከለኛው የኦሮሚያ ክልሎች ዛሬ ሙሉ ቀን ሕዝቡ አደባባይ ወጥቶ ከፍተኛ የሆነ ተቃውሞ ሲያሰማ መዋሉ ተዘገበ:: የዘ-ሐበሻ የመረጃ ምንጮች እንደዘገቡት በምዕራብ ወለጋ መንዲ ከተማ በተደረገው ከፍተኛ ተቃውሞ ሕዝቡ በአደባባይ ጎማዎችን ጭምር በማቀጥል መሪር ተቃውሞውን አሰምቷል:: 


    ይህ በመንዲ ከተማ የተጀመረው ተቃውሞ ወደ መካከለኛው ና ም ዕራብ ወለጋ ከተሞች እየተዛመተ መሆኑ የተሰማ ሲሆን በአካባቢው ከፍተኛ የፌደራል ፖሊሶች መስፈራቸውንም የደረሱን መረጃዎች ያሳያሉ:: በመንዲ ከተማ ሲቀጣጠል የዋለው ተቃውሞ መነሻ በአዲስ አበባ አዲሱ ማስተር ፕላን ዙሪያ መሆኑ ተሰምቷል:: በዚሁ በአዲሱ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ተቃውሞ ዙሪያ ከአንድ ዓመት በፊት በተደረገ ተቃውሞ በአምቦ በስልጣን ላይ ያለው የሕወሓት መንግስት በርካታ ተማሪዎችን መግደሉ ይታወሳል:: የሕወሓቱ ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩት አቶ አባይ ጸሐዬ ከዚህ ቀደም በርካታ ወጣቶች በተቃውሞ ከተገደሉ በኋላ በአንድ ስብሰባ ላይ ባደረጉት ስብሰባ “የአዲስ አበባን አዲሱን ማስተር ፕላን ተግባራዊ እናደርጋለን… የሚቃወሙትንም ልክ እናስገባለን” ሲሉ መፎከራቸውን ዘ-ሐበሻ መዘገቧ አይዘነጋም:: 
   በቅርቡ በኦሮሚያ የሚነሱ ተቃውሞዎችን ለማርገብ በአንዳንድ የኦህዴድ ባለስልጣናት አማካኝነት ለሕዝቡ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን አይካሄድም በሚል ሲነገረው የቆየ ሲሆን ከበስተጀርባ ሌሎች ባለስልጣናት ማስተር ፕላኑን ለማስፈጸም እየተንቅሳቀሱ መሆኑ በኦሮሚያ የተለያዩ ክልሎች እንደገና አደባባይ የወጡ ተቃውሞዎች መታየት ጀምረዋል:: - 

No comments:

Post a Comment