Monday, November 9, 2015

በሰሜን ጎንደር ዞን የልዩ ሃይል አባላት ከህዝቡ ጋር እየተታኮሱ ነው

ጥቅምት ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በሰሜን ጎንደር ዞን በላይ አርማጭሆ በተለይ በማውራ የተጀመረው በህዝብ እና በክልሉ ልዩ ሃይል መካከል የተፈጠረው ግጭት ወደ ታጭ አርማጭሆ የተዛመተ ሲሆን፣ አርሶ አደሩ ከልዩ ሃይሎች ጋር ባደረጉት ተኩስ እስኩን በትንሹ ከ10 ያላነሱ የልዩ ሃይል አባላት ሲገደሉ፣ ከአርሶ አደሮች ደግሞ 6 የሚሆኑት ተገድለዋል። 9 የሚሆኑ የልዩ ሃይል አባላትም ቆስለዋል። የፌደራል ፖሊስ በአካባቢው በብዛት ተሰማርቷል።አርሶአደሮቹ መንገዶችን በመቁረጥ ተሽከርካሪ እንዳያልፍ አድርገዋል፡፡

ከቅማንት ህዝብ ጥያቄ ጋር በተያያዘ ለወራት የቆየው ተቃውሞ ደም አፋሳሽ ሆነ የቀጠለ ሲሆን፣ግጭቱ በቀላሉ እንደማይበርድ ተወላጆች እየገለጹ ነው።በተለያዩ ቀበሌዎች ትምህርት ቤቶች ከተዘጉ ሳምንታትን አስቆጥረዋል።
የቅማንት ህዝብ ላነሳው የራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ የአማራ ክልል በ42 ቀበሌዎች ተግባራዊ እንዲያደርግ ፈቃድ ቢሰጥም፣ ጥያቄውን ያቀረቡት ቡድኖች ደግሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀበሌዎቹ ወደ 126 ከፍ እንዲሉ ፈቅዶልን ሳለ ክልሉ ወደ 42 ዝቅ ሊያደርግብን አይገባም፣ ቀበሌዎችን ይዘን እንደ አዊ ዞን ልዩ ዞን ተብለን እንተዳደር እንዲሁም የታሰሩት ወገኖቻችን ይፈቱ የሚሉ ቅሬታዎችን ያቀርባሉ። አሁን ለተፈጠረው የግጭት መንስኤም በክልሉና በፌዴሬሽን ምክር ቤት መካከል ያለው ልዩነት የፈጠረው ነው ሲሉ ተቃውሞውን የሚያስተባብሩ ስማቸው እንዲገለጥ የማይፈልጉ ሰዎች ያስረዳሉ።
በአካባቢው የሚኖሩት አንዳንድ ዜጎች በበኩላቸው የቅማንት ህዝብ ባህሉና ቋንቋው ተከብሮለት እንዲኖር መጠየቁ ችግር ባይኖረውም፣ ራሳችንን እናስተዳድር በማለት ለመነጣጠል የሚደረገው ሩጫ፣ ህወሃት የአካባቢው ህዝብ በአንድነት ቆሞ ለመብቱ እንዳይታገል ለመከፋፈል የሚጠቀምበት ክስ ነው ይላሉ። አስተያየታቸውን ለኢሳት የሰጡት የቀድሞው የመኢአድ የሰሜን ጎንደር ተወካይ አቶ ያሬድ ግርማ ችግሩን ከጀርባ ሆነው የሚያሽከረክሩት የብአዴን ባለስልጣናት ናቸው በማለት፣ ብአዴን ችግሩን ፈጥሮ መልሶ ደግሞ ችግሩን ያልፈጠረ ለመምሰል በሚወስደው እርምጃ ህዝብ እያለቀ መሆኑን ይገልጻሉ።
የቅማንት ተወላጆች በበኩላቸው ህወሃት ከጀርባቸው እንደሌለ ከአማራ ክልል ውጭ የትም መሄድ እንደማይፈልጉና ጥያቄያቸው የአስተዳደር ብቻ መሆኑን ይናገራሉ። የአካባቢው ተወላጆች ጥያቄዎን ያቀረብነው በሰላማዊ መንገድ ሆኖ ሳለ፣ ጦር መላኩ ተገቢ አይደለም በማለት የመንግስት ወታደሮች የሚወስዱትን እርምጃ እየተቃወሙት ነው።
በሌላ ዜና ደግሞ የአማራ ክልል መሪ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በአስቸኳይ ተጠርተው ወደ አዲስ አበባ ሄደዋል። አቶ ገዱ ሰሞኑን በድርቅ የተጎዱ የምስራቅ አማራ ቦታዎችን ለመጎብኘት ከሚሴ ቢገቡም፣በትላንትናው እለት ከወደ አዲስ አበባ በደረሳቸው አስቸኳይ የስልክ ጥሪ ተደናግጠው ጉብኝቱን አቋርጠው ወደ አዲስ አበባ ከ11፣30 በፊት ድረስ ተብያለሁ በማለት ሄደዋል፡፡ የጉብኝቱ መርሃ ግብር የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደርን ብቻ ሳይሆን የሰሜን ሸዋን ወረዳዎችንም በፕሮግራሙ ያካተተ ነበር፡፡
አቶ ገዱ ወደ አዲስ አበባ ለምን እንደተጠሩ ባይታወቅም፣ ምናልባትም በሰሜን ጎንደር ከሚታየውና ከቁጥጥር ውጭ እየሆነ በመጣው ችግር ከከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ጋር ለመነጋጋር በማሰብ ወይም ከአቶ በረከት ስምዖን ጤና ጋር በተያያዘ በማህበራዊ ሚዲያው ከተለቀቀው ዜና ጋር ተያይዞ ይሁን አይሁን የታወቀ ነገር የለም።

No comments:

Post a Comment