Tuesday, November 17, 2015

ብአዴን ህዝቡን በግዳጅ ሰልፍ እያስወጣ በአሉን እያከበረ ነው

ኀዳር ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-35ኛ አመት በአሉን በማክበር ላይ ያለው ብአዴን ፣ የመንግስት ሰራተኞች ፣ ተማሪዎች፣ ነጋዴዎችና በተለያዩ ሙያ የተሰመራዩት ሁሉ ስራቸውን አቁመውና ድርጅታቸውን ዘግተው በአሉን እንዲያከብሩ ተገደዋል። በበአሉ ላይ ባልተገኙት ላይ የተለያዩ ደረጃ ያላቸው ቀጣቶች እንደሚተላለፍባቸው የድርጅቱ ካድሬዎች ሲቀሰቅሱ መሰንበታቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል። በኮምቦልቻ፣ ደሴ ጎንደርና ሌሎችም ቦታዎች ህዝቡ ለብአዴን ሰልፍ እንዲወጡ ተገደዋል። በተለይ ተማሪዎች በበአሉ ላይ ካልተገኙ በትምህርታቸው ውጤት ላይ አደጋ እንደሚገጥማቸው ተነግሯቸዋል።

በክልሉ ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ ፍተሻም በመካሄድ ላይ መሆኑን ወኪሎቻችን ዘግበዋል። በተለይ በባህርዳር ከተማ መግቢያና መውጫ መንገዶች ፍተሻው አስቸጋሪ በመሆኑ ተጓዦች ምሬታቸውን እየገለጹ ነው።
በክልሉ የተሰማሩ ባለሃብቶችም በኮታ በተመደበላቸው መሰረት ለበኣሉ ዝግጅት የሚሆን ገንዘብ በመዋጮ በግዳጅ እንዲለግሱ እየተደረጉ ነው።
ንቅናቄው በተለይ አስከፊ ረሃብ ባንዣበበት በዚህ ወቅት ከ300 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ በመመደብ እያካሄደ ያለው ፌሽታ ትልቅ ነቀፌታን ካስከተለበት በሃላ የበዓል አዘጋጅ ኮሚቴው በክልሉ የተሰማሩ ባለሃብቶችን በመከፋፈል ስልክ እየደወለ «ይህን ያህል ተመድቦብሃል፣ እስከዚህ ቀን ድረስ መዋጮውን እንድታስገባ» የሚል ቀጭን ትዕዛዝ ሲያስተላልፉና ወጥረው በመያዝ ገንዘብ ሲሰበስቡ ሰንብተዋል፡፡ ይህም የተፈለገበት ዋና ምክንያት በኣሉ ከመንግስት ካዝና ሳይሆን ከባለሃብቱ በተገኘ መወጮ እየተከበረ ነው ለማለት ታስቦ መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
አንድ በባህርዳር በንግድ ስራ የተሰማራ ባለሃብት በድንገት ስልክ ተደውሎ 100ሺ ብር በፍጥነት አስገባ መባሉን ተናግሯል። ይህን ያህል ገንዘብ እንደሌለውና ስራውንም በባንክ ብድር እንደሚሰራ ምላሽ ቢሰጥም «ይህን ሃብት ያገኘኸው በተጋዮች መሰዋዕትነት ነው፣ የሚበጅህ ከድርጅቱ ጎን መቆም ነው» የሚል ማስፈራሪያ ስለደረሰው ተበድሮ ለመክፈል መገደዱን ተናግሮአል፡፡
በአሁኑ ሰዓት በኣሉን ለማክበር ከተለያዩ አካባቢዎችና ክልሎች ወደባህዳር እንግዶች እየጎረፉ ሰሆን ፣ በባህርዳር በርካታ ሆቴሎች አስቀድመው በክልሉ ስለተያዙ መኝታ ማግኘትም አስቸጋሪ እንደሆነባቸው ወደዚያው የተጉዋዙ ታዳሚዎች ገልጸዋል፡፡
የአማራ ክልል ርዕሰ መዲና ባህርዳርን ጨምሮ በአጠቃላይ በክልሉ የሚገኙ የመንግስት ቢሮዎችና ተሽከርካሪዎች በባነሮችና በፖስተሮች የተሞሉ ሲሆን፣ የመንግስት ሠራተኞችም በስራ ሰዓት፣ በመንግስት በጀት በመታገዝ በበዓል ማክበር ስራ ውስጥ ከመወጠራቸው ጋር ተያይዞ መደበኛ የመንግስት አገልግሎት እየሰጡ አለመሆኑ ታውቆአል፡፡ በዘንድሮው ድርቅ በከፍተኛ ደረጃ ከተጎዱ ክልሎች የአማራ ክልል ግንባር ቀደሙ ነው።
ብአዴን 10 አመት የትግል ጉዞውን የሚዘክርበት መጽሃፍ ረቂቅ ኢሳት እጅ የገባ ሲሆን፣ በረቂቁ ላይ አቶ በረከት የተለያዩ አስተያየቶችን ሰጥተውበታል። አቶ በረከት የህዝቡ የዲሞክራሲ፣ የነጻነትና የኑሮ ጥያቄዎች አሁንም ድረስ ያልተመለሱ በመሆኑ፣ ተቃዋሚዎች እንዳይጠቀሙበት በሚታተመው መጽሃፍ ላይ እንዲወጣ ወይም እንዲቀየር አስተያየት ይሰጣሉ። ብአዴን “የህወሃት የአማራ ክንፍ ነው” የሚለውን የተለመደ አገላለጽ ለማስተባበል በመጽሃፉ ውስጥ ሰፊ ሽፋን ተሰጥቶታል። ይህ ከፍተኛ ወጪ ወጥቶበት የሚታተመው መጽሃፍ በእለቱ ለስርጭት ይበቃል ተብሎ ይጠበቃል። ረቂቁን መጽሃፍ የላኩልንን የማተሚያ ቤት ሰራተኞች ኢሳት ከልብ ያመሰግናል።

No comments:

Post a Comment