Wednesday, January 21, 2015

ወያኔ የሚመለመል ወታደር አጣ!

ዳግማዊ አቤ ጉበኛ
ወያኔን የሚከዱ ወታደሮች በየቦታው እየተሰማ ባለበት ባሁኑ ሰዓት የሚመለመል ወታደር መጥፍቱ ምናልባትም ወያኔዎቹ ከፍተኛ የራስ ምታት ሳይሆንባቸው አይቀርም፡፡ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በተደጋጋሚ የአዲስ ቅጥረኛ ወታደር ማስታወቂያ ቢያወጡም፣ አይደለም የሚመለመል ወታደር ቀርቶ የሚመዘገብ ጠፋ፡፡

እናም ይህንን ችግር ለመፍታት ወያኔ አዲስ ዘዴ ቀየሰ፡፡ ከከተማ እስከ ገጠር ቀበሌ፣ በብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ስም አማላይ ማስታወቂያዎችን አስለጠፈ፡፡ ይህ በሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የወጣው ማስታወቂያ የሚመለምለው በሚከተሉት የሙያ ዘርፎች እንደሆነ ይዘረዝራል፡፡
1. ጄኔራል መካኒክ
2. ኤሌክትሪክሲቲ/ ኢንዱስትሪያል ኤሌክትሪክ ሲቲ/
3. ኤሌክትሮኒክ /ማካትሮኒክ/
4. ማሽን ቴክኖሎኪ
5. አውቶ መካኒክ
6. አውቶ ኤሌክትሪክ

የምልመላ መስፈርቱ ‹‹በመከላከያ ሚኒስቴር ለአዲስ ምልመላ ወታደሮች ያስቀመጣቸው የቅበላ መስፈርቶች እንደተጠበቁ ናቸው›› ይላል፡፡ ይህን የማታለያ ዘዴ (አታሎ ወታደር የማድረግ) ወያኔ ብዙ ጊዜ ተጠቅሞበታል፡፡ በኢትዮ­ኤርትራ ጦርነት ጊዜ አስራ ሁለተኛ ክፍል የጨረሱ ተማሪዎችን ‹‹ኑ እናስተምራችሁና ስራ እናስቀጥራችሁ›› ብለው አታለው ከወሰዷቸው በኋላ ጦርነት ውስጥ ማገዷቸው፡፡ ብዙ እናቶችም የደም እንባ አነቡ፡፡ ዘንድሮ ግን ይህ የማታለያ ዘዴ ፈጽሞ ሊሰራላቸው አልቻለም፡ምክንያቱም ይህችን የወያኔ ጨዋታ ህዝቡ በልቷታል፡፡

በገጠር ቀበሌዎች ማስታወቂያውን የለጠፉት አብዛኛውን ፖሊሶች ናቸው፡፡ እግር መንገዳቸውም እለቱ እሁድ ስለነበር፣ የተሰበሰቡትን ገበሬዎች ልጆቻቸውን እንዲሰዱ እና ይህ እድልም እንዳያልፋቸው ሰበካ አድርገው ነበር፡፡ ከሰባኪያን ፖሊሶች አንዱ ያለው ግን በጣም ያስቃል፡፡ እንዲህ ነበር ያለው ‹‹እኔ ይህን እድል ባገኜው ኖሮ፣ ዳግም የተፈጠርሁ ያህል እቆጥረው ነበር›› ነበር ያለው፡፡ ያኔ ሁሉም ገበሬዎች ሳቁልሃ! አንዳንዶቹም ‹‹ታዲያ ለምን አትሄድም?›› ሲሉ አሾፉበት፡፡ ጋሽ ፖሊሱ በመጣበት መንገድ አፍሮ ተመለሰ፡፡

በከተማ ማስታወቂያውን ካድሬዎች ሲለጥፉ የከተማው ወጣቶች ከበው ያዩዋቸው ነበር፡፡ አብዛኛዎቹ ስራ አጥ ስለሆኑ የስራ ማስታወቂያ መስሏቸው ነበር ሰፍ ብለው ለጣፊውን ካድሬ ክብብ ያደረጉት፡፡ ማስታወቂያውን አንብበው እንኳ ሳይጨርሱ ‹‹አንተ ለምን አትሄድም›› ሲሉ አምባረቁበት፡፡ እኒህ ወጣቶችና ማስታወቂያውን የለጠፈው ካድሬ ማታ ካራንቡላ ቤት ተገናኙ፡፡ ስለ ማስታወቂው ወሬ ተጀመረ፡፡ እናም ካድሬው ማንንም ሳይፈሩ ‹‹እብድ ይሂድ እንጂ ማንም እንዲሄድ አልመክርም›› ብለውት እርፍ አሉ፡፡በነገራችን በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ከወጣት እስከ ሽማግሌ ከመንግስት ሰራተኛ እስከ ገበሬዎች የወያኔን የጦር ካምፕ ሳይሆን የአማጺያንን ካምፕ እየተቀላቀሉ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment