Friday, January 9, 2015

ሁለት የኢሳት ጋዜጠኞች በድንበር አካባቢ ያሉ እንቅስቃሴዎችን ለመዘገብ ወደ ኤርትራ መሄዳቸው የበርካታ ኢትዮጵያንን እያነጋገረ ነው።

ታኀሳስ ፴(ሠላሳ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢሳት በትናንት በዘገባው እንዳስታወቀው ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን እና ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም ወደ ኤርትራ ያቀኑት በኤርትራ ድንበር አካባቢ የሚንቀሳቀሱ የ ኢት ጰያ ተቃዋሚዎች እያደረጉት ያለውን እንቅስቃሴ በዓይን
አይቶ ለመዘገብ፤እንዲሁም ከተሳካላቸው በወደፊቱ የኢትዮጰያና የኤርትራ ግንኙነት ዙሪያ የኤርትራ ባለስልጣናትን ቃለ ምልልስ ለማድረግ ነው። ይህን ተከትሎ እጅግ በርካታ ኢትዮጰያውያን ለጋዜጠኞቹ ያላቸውን አክብሮትና አድንቆት በመግለጽ ላይ ይገኛሉ።
እነኚህ ወገኖች ፤ጋዜጠኞቹ- እንደ ጋዜጠኛ በተግባር መሬት ላይ ያለውን ነገር አይተው ለህዝብ ለማሳወቅ ወደ ድንበር ማምራታቸው ፤ ለሙያቸው የተሰጡ መሆናቸውን የሚያመላክት ከመሆኑም ባሻገር – ውሳኔያቸው በሁለቱ ሀገራት ህዝቦች መካከል መልካም መቀራረብና ወንድማችነት እንዲኖር የሚያበረክተው አስተዋጻኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል።
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በየመን መንግስት ለኢህአዴግ ተላልፎ መሰጠቱ ያስቆጣቸው ኢትዮጰያውያን ደግሞ፤ በማህበራዊ ሚዲያዎችም ሆነ ወደ ኢሳት ስልክ በመደወል በሰጡዋቸው አስተያየቶች ፤ጋዜጠኞቹ የወሰዱትን ድፍረት በማድነቅ በሰላም እንዲመለሱ ምኞታቸውን ገልጸዋል። እነኚህኞቹ ጋዜጠኞቹ በሰላም እንዲመለሱ ምኞታቸውን እየገለጹ ያሉት ፤ በሀገር ቤት ያሉ ጋዜጠኞችን ለእስርና ስደት የዳረገውና በኢሳት ክፉኛ የሚበሳጨው የኢህአዴግ መንግስት እንደ አቶ አንዳርጋችው ጽጌ ጋዜጠኞቹን በመንገዳቸው ላይ በገንዘብ እንዳያስጠልፋቸው በመስጋት ነው።
በሌላ በኩል የገዥው ፓርቲ አባላት የሆኑ ካድሬዎች ደግሞ፤ የጋዜጠኞቹ ለዘገባ ወደ ኤርትራ ማቅናት ከተሰማ በሁዋላ ቁጣና ንዴታቸውን ያለመቋረጥ በመግለጽ ላይ ናቸው። በአሁኑ ወቅት ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን እና ፋሲል የኔዓለም በሰላም ኤርትራ ከመግባታቸውም በላይ በነጻነት በመንቀሳቀስ የሄዱበትን ስራ እየከወኑ ይገኛሉ።
ጋዜጠኛ መሳይ በፌስ ቡክ ገጹ አስመራ ከተማን ከሁዋላው አድርጎ በተነሳው ፎቶ ስር ባሰፈረው ጽሁፍ፦<<አስመራ፡ ተራራ ላይ የከተመች፡ ጥንታዊ ገጽታዋን ያለቀቀች ውብ ከተማ። ኢሳት አስመራ ገብቷል፡፡ ሰላማዊውን ትግል በሰፊው እየዘገብን ነው። ዱር ቤታቸው አድርገው በሃይል ህወሀትን ለማስወገድ የተዘጋጁትን ሃይሎች ደግሞ በአካል ተገኝተን ልናያቸው ነው፡፡ባልደረባዬ ፋሲል የኔዓልምም ከአምስተርዳም አስመራ ከቷል። ታሪካዊ ጉዞ ነው፡፡>>ብሏል።
በሚቀጥሉት ቀናት ወይም ሳምንታት ፋሲልና መሳይ በኤርትራ ቆይታቸው ከስፍራው የሚያጠናቅሯቸውን ዘገባዎች በቀጥታ የምናቀርብ መሆኑን ከወዲሁ እናሳውቃለን።


No comments:

Post a Comment