Monday, January 5, 2015

ከኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብ እና የኢትዮጵያ ኣርበኞች ኣንድነት ንቅናቄ የተሰጠ መግለጫ

ጀግናው የኢትዮጵያ ህዝብ ከወራሪ ሃይሎች ጋር ተፋልሞ ድል ያስመዘገበው ለነጻነቱ በሚሰጠው ከፍተኛ ዋጋ ምክንያት ነው። የዚህ ታላቅ ህዝብ ተጋድሎ ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለመላው ኣፍሪካ ህዝብ የነጻነት ፋና ወጊ ሆኗል።

ይህ ለነጻነት የተከፈለ ትግልና ዉጤቱ እንዲሁ በቀላል ነገር የመጣ ኣልነበረም። ሁሉም የኢትዮጵያዊያን ልጆች ዘር ሃይማኖት ብሄር ቀለም ሳይለዩ ባንዲት ባንዲራና ባንዲት እናት ኣገር ኢትዮጵያ ስም ተሰባስበው ኣንድ ልብ ኣንድ ኣላማ ይዘው ስለታገሉ እንጅ። በዚህ ምክንያትም የኣገራችን መላው ህዝብ በየትኛዉም ቦታ እራሳቸዉን ቀና ኣድርገው የሚሄዱ ነበሩ። በኣሁኑ ወቅት ግን መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ከመቸዉም ጊዜ በከፋ ሁኔታ የነጻነት እጦት ዉስጥ ተዘፍቆ ይገኛል። ያ ነጻነት የለመደ ህዝብ !ያ ተባብሮ በሰላም መኖር ልማዱና ባህሉ ያደረገ ኩሩ ህዝብ! ዛሬ ግን በነጻነት እጦት ስር ወድቆ ከኣኩሪ ታሪኩ ጋር ወደታች እየሰጠመ ይገኛል። ወያኔ ኢህኣዴግ በዘራው መርዝ ምክንያት እርስ በርሱ ተለያይቶና ተፈራርቶ እንደጠላት እየተያየ ይገኛል።


ከሃያ ሶስት ኣመት በላይ ሰላም ኣጥቶ ነጻነት እንደተጠማ ኑሮዉን እየገፋ ነው የሚታየው። በህወሃት ኣገዛዝ እየተንገፈገፈ ቢሆንም ተባብሮ ግን ከላዩ ላይ የተሸከመዉን የመከራ ሸክም ሊያራግፈው ያልቻለው በከፋፋይ ወያኔ መራሽ የከፋፍለህ ግዛው ፖሊሲ ገመድ ተጠፍሮ ስለተያዘ እንደሆነ ድርጅታችን ያምናል። ለዚህ መፍትሄዉ ደግሞ የተባበረ ትግል እንደሆነ በጽእኑ እናምናለን።

የነጻነት እጦት የወለዳቸውና የኢትዮጵያን ህዝብ ከጭቆና ቅንበር ለማላቀቅ የሚታገሉ በርካታ ድርጅቶች እንዳሉ የሚታወቅ ነው። የትግላቸው ዉጤት ግን ግቡን ኣልመታም። ሁላችንም ታጋይ ድርጅቶች ለምን ስንል ራሳችንን የምንጠይቅበት ወቅት ላይ እንዳለን የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብ ያምናል። የዚህ ጥያቄ መፍትሄ ኣቅጣጫ ደግሞ ወደ ኣንድነት የሚወስደን ይሆናል። ያለ ኣንድነት የቱንም ያህል ብንታገል የምንፈልገዉን ዉጤት ልናመጣ እንደማንችል ያሳለፍናቸው የትግል ጊዜያቶች ኣሳይተዉናል።

ይህን የተገነዘበው የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብ\EPPFG\ የሰሜንአሜሪካ የኢትዮጵያ አርበኞች አንድነት ንቅናቄ /EPUM/ ጋር በጋራና በትብብር ለመስራት ከስምምነት ላይ ደርሷል። ታህሳስ 20 \2014 በጀርመን ኑረንበርግ ከተማ በተካሄደው የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብ ኣምስተኛ ኣመት የምስረታ በኣል ላይ የሁለቱ ድርጅቶች ባንድ ኣመራር ጥላ ስር መጠቃለላቸው ይፋ ሆኗል።

የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብ ሊቀ መንበር የሆኑት ኣቶ ልኡል ቀስቅስ የዉህደቱን ኣስፈላጊነት ኣስመልክተው የሚከተለዉን ብለዋል:-

<<ኢትዮጵያ ዉስጥ ሰላም ዴሞክራሲና ልማት ሰፍኖ ማየት የምንሻ ሁላችንም ኣገር ወዳድ የትግል ድርጅቶች እስካሁን ባካሄድናቸው የትግል እንቅስቃሴወች የምንፈልገዉን ዉጤት ማምጣት ኣልቻልንም። ለዚህም ዋናው ምክንያት ተባብረን ኣለመታገላችን ነው። ይህም ለወያኔ ምቹ ሁኔታን ፈጥሮለታል። ካሁን በሁዋላ ግን ኣካሄዳችንን ቆም ብለን ኣይተን በመተባበር ኣምባ ገነኑ ስርኣት እንዲወገድ ማድረግ መቻል ኣለብን። ከዚያ በተረፈ ምርጫ በመጣ ቁጥር የምናደርገው እንቅስቃሴና የተናጠል ትግል የትም እንደማያደርሰን ልንገነዘብ ይገባል። የኢትዮጵያ ህዝብ ኣርበኞች ግንባር ዘብና የኢትዮጵያ ኣንድነት ንቅናቄ ያደርጉት ዉህደት ፈር ቀዳጅ ነው >> ብለዋል።

በዉህደቱ ላይ የተገኙት የሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ አርበኞች አንድነት ንቅናቄ /EPUM/ ሊቀ መንበር የሆኑትአቶ ጥላሁን ገላው በበኩላቸው በዛሬው እለትም የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ዘብ እና የኢትዮጵያ አርበኞች አንድነት ንቅናቄ አብረው ለመስራት መስማማታቸውን ይፋ አድርገዋል። ስለዚህ በኢትዮጵያ አንድነት ከሚያምኑ ጋራአብሮ የመስራት አላማ እንዳላቸው ያረጋገጡት የኢትዮጵያ አርበኞች አንድነት ንቅናቄ ሊቀ መንበር ሌሎች ድርጅቶች፣ ቡድኖች፣ ግለሰቦችና በብሄር ደረጃ የተደራጁ ድርጅቶች በጋራ ለመስራት ወቅቱ ስለሚያስገድድ በጥምረት ለመስራት ከተስማሙት ድርጅቶች ጋር ለመስራት እንዲመጡ ጥሪ አድርገዋል::

በመላው ኣለም የምትገኙ የድርጅታችን ኣባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያን የሁለቱን ድርጅቶች ዉህደት ተገንዝባችሁ ከጎናችን እንድትቆሙና ኣስፈላጊዉን ትብብር እንድታደርጉ እንጠይቃለን።

ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment