Monday, May 9, 2016

የማላዊ መንግስት ያሰራቸውን ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ የሚያስችል ገንዘብ ማጣቱ ተዘገበ።

ሚያዚያ ፩(ግንቦት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ዘ ሰን ዴይ ታይምስ እንደዘገበው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2015 ያለህጋዊ ወረቀት ወደ ማላዊ የገቡ 40 የሚሆኑ ህጻናት ኢትዮጵያውያን በሉሊዌንጌ በሚገኘው የካቸረ ጂቬኒለ እስር ቤት ታስረው ይገኛሉ።
ኢትዮጵያውያኑ ወደ ደቡብ አፍሪካ እንደሚያደርሷቸው ቃል የገቡላቸው የህገ- ወጥ አሻጋሪዎችና ደላሎች ተጠቂዎች መሆናቸውን ጋዜጣው ጠቅሷል።
ማላዊ በክፍለ አህጉሩ ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር ለሚደረጉ እንዲህ ያሉ እንቅስቃሴዎች እንደ መሻገሪያ እንደምታገለግል ይታመናል። ይሁንና የማላዊ መንግስት በገንዘብ እጥረት ሳቢያ ኢትዮጵያውያኑን ወደ ሀገራቸው ለመመለስ እንደተቸገረ ተገልጿል።
ኢትዮጵያውያኑን በአየር ትራንስፓርት ወደ ሀገራቸው ለመመለስ 16 ሺህ ዶላር ያስፈልጋል።ህጻናቱ ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሄድ ካላቸው ፍላጎት በመነሳት በራሳቸው መንገድ ከኢትዮጵያ ኬንያ፣ከኬንያ ታንዛኒያ ከገቡ በኋላ በህገ ወጥ አሻጋሪዎቹ ይወሰዳሉ።
ይሁንና እንደ ጋዜጣው ዘገባ፤ ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች ቢያዙም፤ ህገ ወጥ አሻጋሪዎቹ ተሰውረዋል። አልፎ አልፎ አንዳንድ ህገወጥ አሻጋሪዎች የፍርድ ቤት ቅጣታቸውን ከጨረሱ በኋላ በተመሣሳይ መንገድ ህገ ወጥ ስደተኞች ሊያሻግሩ ሲሉ ድንበር ላይ የተያዙበት አጋጣሚ እንዳለ ተመልክቷል።
በማላዊ የሰብ ዓዊ መብት ኮሚሽን የህጻናት መብት ጥበቃ ዳይሬክተር ኖሪስ ችርዋ በህገወጥ መንገድ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሊሄዱ ሲሉ የተያዙት ህጻናት የተጣለባቸውን ቅጣት እንደፈጸሙ ተናግረዋል።
“የህጻናቱ ቤተሰቦች ልጆቻቸው ደቡብ አፍሪካ እንዲሄዱላቸው ያላቸውን ዕቃ እየሸጡ ከ2ሺህ እስከ 4 ሺህ ዶላር ይከፍላሉ፤ አንዳንዶቹ እንደ ሁኔታው ማላዊ ለመግባት ብቻ እስከ አንድ ዓመት ይፈጅባቸዋል።” ብለዋል ዳይሬክተሯ።
ህጻናቱ ወደ ሀገራቸው ኢትዮጵያ እስኪላኩ ድረስ በሰብዓዊ መብት ኮሚሽኑ የህጻናት ጉዳይ ግምገማ ቦርድ ጊዜያዊ መጠለያ እያፈላለገላቸው እንደሆነ ዳይሬክተሯ ገልጸዋል። “የመንግስት ፍላጎት ህጻናቱ ቅጣታቸውን እንደጨረሱ ወደ ትውልድ ሀገራቸው መላክ ነበር;ይህን ለማድረግ ግን ገንዘብ አልተገኘም።መንግስት ከዚህም በላይ በሌሎች ሀገራት እንደሚደረገው ሁሉ ህገ ወጥ ስደተኞችን በወህኒ ከማቆየት ውጪ ለእነሱ የሚሆን የተለየ መጠለያ አላስገነባም።ለዚህም ነው ህጻናቱ በካቻረ ወህኒ ቤት እንዲቆዩ የተደረገው”ብለዋል- ኖሪስ ችርዋ።
የዓለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት የማላዊ ኃላፊ ስቲፈን ትሮቸር ባለፈው መስከረም በማላዊ እስር ቤት ለሚታየው አስጨናቂ ሁኔታ የረዥም ጊዜ መፍትሄ እንዲፈለግለት አሣስበው ነበር።
“ከአስር ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ታሳሪዎች መካከል አንዱ ህጻን የመሆኑ ነገር እጅግ ይረብሸናል፤ ህገ ወጥ ስደት ህጻናቱን ለበሽታ፣ለጉልበት ብዝበዛ ፣ለአደጋና ለእስር እያጋለጣቸው ነው።የተጨናነቁት የማላዊ እስር ቤቶች ለዚህ ምስክሮች ናቸው።” ብለዋል- ስቲፈን።
በህገ ወጥ መንገድ ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመግባት የሚፈልጉ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን በየ ዓመቱ ህይወታቸውን አደጋ ላይ እየጣሉ እንደሆነ የሰን ዴይ ታይምስ ዘገባ ያመለክታል። ማላዊ፦”የትራንስፖርት ገንዘብ ስለሌለኝ ወደ ሀገራቸው ልመልሳቸው አልቻልኩም” ባለቻቸውና በእስር እየተሰቃዩ በሚገኙት ህጻናት ኢትዮጵያውያን ዙሪያ እስካሁን የኢትዮጵያ መንግስት የሰጠው አስተያዬት የለም። ይልቁንም ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ለልማት ገንዘብ ለማሰባሰብ በሚል ኢትዮጵያውያን በስደት ወደሚገኙባቸው ሀገራት በመሄድ ስብሰባ እያደረጉ ይገኛሉ።
በሌላ ዜና ደግሞ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲያቀኑ የነበሩ 34 ኢትዮጵያዊያን ስደተኞችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን የዛንቢያ የድንበር ፓሊስ አስታውቋል። ኢትዮጵያዊያኑ ስደተኞች በሕገወጥ መንገድ መነሻቸውን ታንዛኒያ በማድረግ የዛንቤዚን ወንዝ ተከትለው ወደ ዝንባብዌ አቆራርጠው ሲገቡ በናኮንዳ ድንበር አቅራቢያ ተይዘዋል።
በፓሊስ ቁጥጥር ስር ከዋሉት ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ውስጥ አንዱ በአካባቢው ነዋሪዎች ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞበታል። የድንበር ፓሊስ ቃል አቀባይ የሆኑት ሙላታ እንዳሉት ከሆነ ጉዳተኛው ኢትዮጵያዊ የሕክምና እርዳታ እየተደረገለት መሆኑንም አስረድተዋል።
ባለፈው ወርም 19 ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ተይዘው አንድ ሽህ የዛንቢያ ክዋቻ ወይም የስድስት ወር እስራት እንደተፈረባቸው ሉሳካ ታይም ዘግቧል።
የገዥው ፓርቲ ባለስልጣናት ኢትዮጵያ ታአምራዊ የምጣኔ ሃብት እድገት አምጥታለች እያሉ በመገናኛ ብዙሃን ዘወትር ቢናገሩም ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ግን ሕይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው በአራቱም ማእዘናት መፍለሳቸውን ቀጥለዋል። እስካሁን ድረስ በኢትዮጵያ መንግስት ኤንባሲም ሆነ ቆንስላ በኩል በእስር ላይ ያሉትን ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ጉዳይ የሚከታተል አልተገኘም።

No comments:

Post a Comment