Tuesday, May 17, 2016

ምርጫ ቦርድ የዶ/ር በየነ ጴጥሮስን ኢዴሃህን ጨምሮ 14 ፓርቲዎችን ከግንቦት 5 ቀን ጀምሮ መሰረዙን አስታወቀ

ግንቦት ፱(ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከቦርዱ የተሰጠው መግለጫ እንደሚያመለክተው ፓርቲዎቹ በመተዳደሪያ ደንባቸዉ መሠረት ጠቅላላ ጉባኤ የሚያካሂዱበት ጊዜ ያለፈ በመሆኑና የሥራ ጊዜያቸው በተጠናቀቀው አመራሮች ምትክ አዲስ የአመራር አባላትን መርጦ ወዲያውኑ ለቦርዱ ባለማሳወቃቸው፣ በኦዲተር የተረጋገጠና በግንባሩ መሪ የተፈረመ የሃብትና እዳ ሰነድ የጽሑፍ ሪፖርት ባለማቅረባቸው፣ ፓርቲው ያለውን ዋና ጽሕፈት ቤት እና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች አድራሻ፣ የጽሕፈት ቤቶቹን ኃላፊዎች ወይም ተወካዮች ለቦርዱ በጽሑጽ ባለማሳወቅ፣ እንዲሁም በሚመለከተው ሕጋዊ አካል የተረጋገጠ የሞያ ብቃት ያለው በፓርቲው የተሾመ የውጭ ኦዲተርና የተሾመው ኦዲተር ሹመቱን መቀበሉን በፊርማው ያረጋገጠበት ሰነድ ባለማቅረባቸው ፓርቲዎቹ መሰረዛቸውን ጠቅሷል።

የተሰረዙት ፓርቲዎች የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ኅብረት /ኢዴኃኅ/፣የኮንሶ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ ኅብረት /ኮሕዲኅ/፣ የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ ፓርቲ /ኢአምፓ/፣ ባሕረወርቅ መስመስ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ባመሕዴድ/፣ የጠንባሮ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ኅብረት /ጠሕዴኅ/፣ የሶዶ ጎርደና ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ሶጎሕዴድ/፣ የጋሞ ጎፋ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ አንድነት /ጋጎሕዴአ/፣ የሐረሪ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /ሐሕዴፓ/፣ የጉራጌ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ግንባር /ጉሕዴግ/፣ የሶማሌ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ቅንጅት /ሶዴኃቅ/፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች አንድነት /ደኢዴኃአ/፣ የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ኅብረት /ጋዴኅ/፣ የሀዲያ ብሔራዊ አንድነት ዲሞክራሲያዊ ድርጅት /ሀብአዴድ/፣ የአፋር ብሔራዊ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር /አብአዴግ/ ናቸው።

No comments:

Post a Comment