Friday, May 27, 2016

“ህዝቡ ከኢህአዴግ መሪዎች ይልቅ በውጭ ለሚገኙ የፖለቲካ መሪዎች እውቅና እየሰጠ ነው” ሲል የደህንነት መስሪያ ቤቱ አስታወቀ

ግንቦት ፲፱ (አሥራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ኢህአዴግ 25ኛ አመት በአሉን እያከበረ በሚገኝበት ወቅት እያደረገ ባለው ግምገማ የደህንነት መስሪያ ቤቱ ለስርአቱ አደጋ ሊፈጥሩ ይችላሉ ያላቸውን ጉዳዮች ለውይይት ከማቅረብ ባሻገር ፣ ህዝቡ በአገር ውስጥ ላሉ የኢህአዴግ ባለስልጣናት ከሚሰጠው እውቅና ይልቅ በውጭ አገር ለሚገኙ የተቃዋሚ መሪዎች እየሰጠ በመምጣቱ የስደት መሪዎችን እስከመሾም ተደርሷል ብሎአል ።

የደህንነት እና መረጃ ክፍል ባቀረበው ጥቅል ግምገማ የኤርትራ መንግስት የሚካሄደውን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ስልክ ጠልፎ በማዳመጥ በኩል ውጤታማ ስራ መሰራቱን ገልጿል። “ይሁን እንጅ” ይላል ሪፖርቱ “በሰሜን ጎንደር እና በሱዳን ድንበሮች አካባቢ ብዙ ስራዎችን ለመስራት ቢታቀድም ብቃት ያለው ስራተኛ ባለመገኘቱ የታቀደውን ያህል ስራ መስራት ሳይቻል ቀርቷል፡፡”

“አርበኞች ግንቦት ሰባት በመከላከያ ሰራዊታችን ውስጥ ሰርጎ ገብቷል የሚል በተለይም ተመላሽ የሰራዊት አባላት ድርጅቱን ለመቀላቀል ፍላጎት እያሳዩ ነው የሚል ማስረጃ አልባ መረጃዎች አሉ” የሚለው የደህንነት መስሪያ ቤቱ፣ አሳሳቢው ጉዳይ ህዝቡ በውጭ ለሚኖሩ የፖለቲካ መሪዎች እውቅና እየሰጠ በመምጣቱ የስደት ፖለቲካ መሪዎችን እስከመሾም ደርሷል ብሎአል።
በሀገር ውስጥ በህጋዊነት ተመዝግበው በውጭ ከሚገኙ ተቃዋሚዎች ጋር ግንኙነት እየፈጠሩ ረብሻ የፈጠሩ ኃይሎችን በቁጥጥር ስር ማዋል ቢቻልም፣ አሁንም የሚቀሩ ስራዎች አሉ ይላል። ችግሩን ለመቋቋም ውስጥን ማጥራት ተገቢ መሆኑንም አስጠንቅቋል።
የደህንነት ክፍሉ ለኢህአዴግ ፈተና ይሆናሉ የሚላቸውን አምስት ጉዳዮችን በማንሳት ለውይይት አቅርቧል።ኢህአዴግን ፈተና ላይ ሊጥሉት ይችላሉ ተብለው በኢንፎርሜሽን መረብ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሻለቃ ቢኒያም ተወልደ የቀረቡት መላምቶች-
“የመከላከያ ሠራዊት መፈንቀለ መንግስት ለማድረግ ከተደራጀ፣ የተራዘመ የገጠር የትጥቅ ትግል ከተካሄደ ፣ ነጋዴው እና ህዝቡ ግብር ለመክፈል ፈቃደኛ መሆን ካልቻለ እና ባለሃብቱ በገንዘቡ ተቃዋሚዎችን ከደገፈ፣ ማህበረ ቅዱሳን እና የእስልም ድርጅቶች በተመሳሳይ ሰዓት ውስጥ ወደ አመፅ ከገቡ እንዲሁም የታጠቁ ሐይሎች ወደ ህቡዕ አደረጃጀት ገብተው መምራት እና ሃይላቸውን ማሰመራት ከቻሉ” የሚሉት ናቸው።
“የውጭ ሃይሎች ለተደራጁ ኃይላት የገንዘብ እና የመሳሪያ ድጋፍ ካደረጉ እንዲሁም የተደራጁ የሲቪክ ማህበራት ለፖለቲካዊ ለውጥ ከሰሩ” የሚሉ ተጨማሪ መላምቶች የማዳበሪያ ሃሳቦች ሆነው ቀርበዋል።
ምንም እንኳ የደህንነት መስሪያ ቤቱ ስጋቶችን ለይቶ ያስቀመጠ ቢሆንም፣ ስጋቶቹ ምን ያክል ተጨባጭነት እንዳላቸው ወይም ምን ያክል ተግባራዊ ሊሆኑ እንደሚችሉ ዘርዝሮ አላቀረበም። ኢህአዴግ በማድረግ ላይ ባለው የአመራር ግምገማ ደግሞ ነባሩን አመራር የሚተካ ብቁ አመራር አለመፈጠሩን ገልጿል።
“የኢህአዴግ የትግል ዘመን ታጋይ እና አታጋዮች ጊዜ እያለቀ ነው፡፡ በትውልድ የመተተካት ስርዓት ውጤታማነት እየቀጠለ አይደለም” በማለት ነባር ታጋይ አመራሮች በውይይቱ ላይ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
“ትግሉን በጎጥ እና በቀበሌ አስተዳደር ለመምራት የተሄደው እርቀት እጅግ ስኬታማ ቢሆንም፣ ስርዓቱን ለማስቀጠል እንጅ፣ ከታጋዮች ዘመን በኃላ የተረጋጋ የፖለቲካ ስርዓት ለመፍጠር ምቹ መደላድል አልተሰራም” የሚል አስተያየተም በታጋዮች ቀርቧል፡፡
የጠ/ሚኒስትሩ የፖሊሲ ጉዳይ አማካሪው አቶ አባይ ፅሃየ በበኩላቸው “አዳዲስ ታጋዮችን የማምጣት እና የማስተዋወቅ ስራ ባለመኖሩ ፤ ተተኪ የማፍራቱ ጥረት የከሸፈ ነው “ ያሉ ሲሆን፣ ከዩኒቨርስቲ ጀምሮ እስከ ቀበሌ እና ከፍተኛ የፖለቲካ አስተዳደር ድረስ ሰዎች በተወለዱበት አካባቢ እንዲመሩት መደረጉ ለሀገሪቱ እድገትም ሆነ ለኢኮኖሚያዊ ለውጥ አስተሳሰብ መዳከም የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል” ሲሉ አክለዋል።
አንድ ነባር ታጋይ “ ለምሳሌ ሳሞራ ቢሞት ማን ሊተካው ነው? ሰራዊቱን ሊያፀናው የሚችለውስ ማን ነው?” የሚል ጥያቄ አንስተው የመተካካቱ ሂደት ችግር እንዳለበትና ለወደፊቱ ፈተና መደቀኑን ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment