Tuesday, May 17, 2016

በማጀቴ ከተማ የተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ እንደቀጠለ ነው

ግንቦት ፱(ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በሰሜን ሸዋ ዞን በአንጾኪያ ገምዛ ወረዳ የሚገኙ የማጀቴ ንኡስ ወረዳ ነዋሪዎች የገምዛ ወረዳ ይመለስልን በሚል የጀመሩት ተቃውሞ እየሰፋ መሄዱን ተከትሎ የመንግስት አመራሮችና ሰራተኞች አካባቢውን ለቀው ወደ ዋናው ከተማ ሄደዋል።

ግንቦት3 ቀን 2008 ዓም የክልሉ የፍትህ ሃላፊና የክልሉ የህዝብ ግንኑነት ተጠሪ ወደ አካባቢው ከተንቀሳቀሱና ህዝቡን ካነጋገሩ በሁዋላ፣ የህዝቡ ጥያቄ ተቀባይነት እንደሌለው በመግለጻቸው፣ በእለቱ ከፍተኛ ተቃውሞ ተነስቶ ነበር። ግንቦት3 የተካሄደውን ተቃውሞ ተከትሎ አካባቢው የጦር ቀጠና መስሎ መዋሉን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ የቀበሌው ሊቀመንበር የሆኑት አቶ አባቡ እንዲሁም የፖሊስ አዛዡ ኢንስፔክተር ሸዋቀናው ከአካባቢው ለቀው ወጥተዋል። ህዝቡ ወደ ሊቀመንበሩ ቤት በማምራት ንብረታቸውን ሙሉ በሙሉ አውድሟል። ከግንቦት 5 ጀምሮ ደግሞ የህዝቡ ተቃውሞ በማዬል ላይ ሲሆን ፣ የተደራጁ ወጣቶች ፣ ከመምህራንና ከጤና ባለሙያዎች ውጭ ሌሎች የመንግስት ሰራተኞች ከአካባቢውን ለቀው እንዲወጡ አድርገዋል። በንኡስ ወረዳዋ የሚገኙት የ6ቱም ቀበሌዎች ወጣቶች የመንግስት ሰራተኞችን ከአካባቢያቸው ካስወጡ በሁዋላ ራሳቸውን በራሳቸው በማስተዳደር ላይ መሆናቸውን ነዋሪዎች ተናግረዋል። ወጣቶቹ “ በወያኔ አገዛዝ ልማት አላየንም፣ በቅኝ ግዛት ውስጥ ነው ያለነው ፣ ነጻነታችንንና መብታችን ያጣን ነን፣ በውክልና የተቀመታችሁ አመራሮች አንፈልጋችሁም፣ ህዝብ አልወከላችሁም፣ ከአካባቢያችን ውጡልን “ የሚሉ መፈክሮችን አሰምተዋል።
ቁጥራቸው 30 ሺ የሚደርስ የአካባቢው ነዋሪዎች ሚያዚያ 2 ቀን 2008ዓም የተቃውሞ ሰልፍ ማድረጋቸው ይታወቃል።
በተመሳሳይ ዜና በደንቢያ የቴክኒክና ኮሌጅ መምህራን የጀመሩት ተቃውሞ ለሶስተኛ ቀን ቀጥሎአል። ተቃውሞው ከሃለፊነት ከተነሱት የኮሌጁ ሃላፊዎች ጋር በተያያዘ የተጀመረ ቢሆንም፣ መምህራኑ ጥያቄው መሰረታዊ የሆነ የመብት ጥሰት የታየበት በመሆኑ መብታችን እስካልተከበረ ድረስ ስራ አንጀምርም እያሉ ነው።

No comments:

Post a Comment