Monday, May 23, 2016

በኢትዮጵያ ያለው የፓለቲካ ምኅዳር መጥበቡንና የሰብዓዊ መብት ጥሰቱ መባባሱን አምነስቲ ኢንተርናሽናል አስታወቀ

ግንቦት ፲፭ (አሥራ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሆነው አምነስቲ ኢንተርናሽናል ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገራት ውስጥ ባደረገው ጥናታዊ ሪፓርት፣ በኢትዮጵ ውስጥ ያለው የሰብዓዊ መብት አያያዝ እየከፋ መምጣቱን ጠቁሟል። ድርጅቱ በኢትዮጵያ የአንድ ፓርቲ የበላይነት መንገሱንና የፓለቲካ ምኅዳሩ መፈናፈኛ በሌለው ሁኔታ በአንባገነኑ ኢሕአዴግ ብቸኛ ቁጥጥር ስር መዋሉን ገልጿል።

ባለፈው ዓመት ተካሂዶ በነበረው ነጻና ገለልተኝነት ባልተንጸባረቀበት የምርጫ ውድድር በተወካዮች ምክር ቤት ካሉት 547 መቀመጫዎች ውስጥ ሙሉ በሙሉ በገዥው ፓርቲ መያዛቸው የጸረ ዴሞክራሲያዊ ባህሪውን ያሳያል ብሏል ድርጅቱ። በኢትዮጵያ የመጻፍ፣ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፎችን የማድረግ ዓለምአቀፍ ድንጋጌዎች ተጥሰው ዜጎች በአፈና አገዛዝ ውስጥ መሆናቸውን ያተተው መግለጫው፣ አገሪቱ ለሲቪክ ማኅበረሰቡ የማትመች አገር ናት ብሏል።
በወርልድ ጀስቲስ ፕሮጀክት ጥናት መሰረትም በፍትሕ እጦት ከዓለም ካሉት 102 አገራት ውስጥ 91ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝና ፍሪደም ሃውስ በበኩሉ ኢትዮጵያ ፍጹም አንባገነንነት የነገሰባት ”ነፃ ያልሆነች አገር”ሲል ከሰባት መመዘኛዎች ስድስቱን የማታሟላ አገር ናት ሲል አስቀምጧታል።
ጋዜጠኞችን በማሰር የመናገር መብት የምታፍነው ኢትዮጵያ፣ በጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ላይ 18 ዓመታት መፈረዱን እና ልጁ ናፍቆት እስክንድር በእስር ቤት መወለዱን አስታውሶ ይህን ዓይነት ዘግናኝ ግፍ በብዙ የአገሪቱ ጋዜጠኞች ላይ ይፈጸማል ብሎአል። የኦሮሞ ፌደራሊስት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ፣ እንዲሁም የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት ኦኬሎ አኳይን የመሳሰሉ የፓለቲካ ፓርቲ አባላት ከሕግ ውጪ ተፈርዶባቸው በወሕኒ ቤት እየማቀቁ እንደሚገኙ ሪፖርቱ አመልክቶ፣ የኢትዮጵያ ገዥዎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ከመፈጸም እንዲታቀቡ ጥሪውን አቅርቧል።

No comments:

Post a Comment