Monday, May 23, 2016

በአዲስ አበባ የመንግስት ባለስልጣናትን መኖሪያዎች የሚያሳዩ ተጨማሪ ቪዲዮች ቀረቡ ( ሪፖርታዥ )

ግንቦት ፲፭ (አሥራ አምስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአዲስ አበባ እና በመላው አገሪቱ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች የኢህአዴግ ሹመኞች በራሳቸውና በዘመዶቻቸው ስም ያስገነቡዋቸው ህንጻዎች የህዝብ መነጋገሪያ አጀንዳ ከሆኑ ውለው አድረዋል። በተቃራኒው ጥረው ግረው የሰሩዋቸው ቤቶች ህገወጥ ተብለው ምንም አይነት ካሳ ሳይከፈላቸው ወይም ተገቢው መኖሪያ ቤት ሳይሰጣቸው በጎዳና ላይ ላስቲክ ዘርግተው የሚኖሩ ዜጎች እየተበራከቱ ነው።
ሰሞኑን በቦሌ ክፍለከተማ ከታየው የቤት ማፍረስ ጋር በተያያዘ ቁጥራቸው ከ8 ያላነሱ ሰዎች በጸጥታ ሃይሎች መገደላቸውን የአይን እማኞች እየቀረቡ በኢሳት ላይ ቢናገሩም፣ መንግስት የቆሰሉ እንጅ የሞቱ ሰዎች የሉም የሚል ማስተባበያ ሰጥቷል።
ቤቶቻቸው የሚፍረሱባቸው ሰዎች እንኳንስ በዜግነት መብታቸው ለወደመባቸው ንብረት ተገቢውን ካሳ ሊያገኙ ወይም ተተኪ ቤት ሊሰጣቸው ቀርቶ ንብረታቸውን እንኳን ማውጣት መከልከላቸው ስፍራው ድረስ በመሄድ በቪዲዮ ቀርጾ የላከልን ወኪላችን ገልጿል።
መንግስት የጨረቃ ቤቶች የሚባሉት ተሰርተው እስኪጠናቀቁ ዝም ብሎ ከተመለከተ በሁዋላ፣ ቤቶቹ ተሰርተው ሰዎች ኑሮአቸውን አንድ ብለው ሲጀምሩ ለምን እርምጃ ይወስዳል የሚለው ጥያቄ በቂ መልስ ሳይገኝለት፣ መንግስትም ለጥፋቱ ሃላፊነት ሳይወስድ ችግሩ ቀጥሎአል።
ድሃ ዜጎች ቤቶቻቸው ከፈረሱባቸው በሁዋላ በቦታው ላይ ህንጻዎችን የሚገኑበት በአብዛኛው የመንግስት ባለስልጣናት እና ከእነሱ ጋር ንክኪ ያላቸው ሰዎች መሆናቸው በህዝቡ ውስጥ እየተባባሰ ለመጣው ቅራኔ ሌላው ምክንያት ነው።
ኢሳት በተለያዩ ጊዜያት የመንግስት ባለስልጣናት እና ከእነሱ ጋር ቀረቤታ ያላቸው ሰዎች የሚያስገነቡዋቸውን ህንጻዎች ይፋ ሲያደርግ ቆይቷል። በአገሪቱ ውስጥ ከተንሰራፋው የሙስና ስፋትና ከተፈጠረው ኔትወርክ አንጻር የትኛው ድርጅት በትክክል የማን እንደሆነ በአሁኑ ጊዜ ለይቶ ለመናገር አስቸጋሪ ቢሆንም፣ የግንባታ መሃንዲሶች ከስራቸው ጋር በተያያዘ የሚያገኙትን መረጃ ለኢሳት በየጊዜው በማካፈል መረጃው ለህዝብ ይፋ እንዲሆን እያደረጉ ነው።
በርካታ የመንግስት ባለስልጣናት የሚኖሩበት ሰፈር ጃክሮስ እየተባለ የሚጠራው አካባቢ ሲሆን፣ በዚህ አካባቢ የሚታዩት መኖሪያ ቤቶች እጅግ ዘመናዊ ከመሆናቸው አንጻር አካባቢው በምእራቡ አለም ያለ እንጅ ከ20 ሚሊዮን በላይ ህዝብ በተራበባት አገር ያለ ወይም ቤቶቻቸው በቡል ዶዘር የሚፍረስባቸው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ድሆች በሚኖሩባት አገር ያለ አይመስልም ።
ባለስልጣኖቹ እና ካድሬዎቹ ከሰሩዋቸው መኖሪያ ቤቶች በተጨማሪ መንግስት ከሚከፍላቸው ወርሃዊ ደሞዝ በብዙ እጅ የሚልቅ ገቢ የሚያስገቡላቸውን የንግድ ድርጅቶች ሰርተው ያስተዳድራሉ። ብዙዎቹ ባለስልጣናት ቤቶቻቸውን በስማቸው ከማስደረግ ይልቅ በባለቤቶቻቸው፣ በልጆቻቸው ወይም በቅርብ ዘመዶቻቸው ማስመዝገባቸው የሚደረሱን መረጃዎች የሚያመለክቱ ቢሆንም፣ ባለስልጣኖቹ በተዘዋዋሪ መንገድ ከመሃንዲሶች ጋር በሚያደርጉት የስራ ግንኙነት፣ ህንጻዎቹ የእነሱ መሆናቸውን ለማወቅ እንደሚቻል ማህንዲሶች ይናገራሉ።
እነዚህ ለህንጻቸው ሌላ ስያሜ ሰጥተው ፣ ከጀርባ በመሆን ክትትል ከሚያድርጉት መካከል የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር የአቶ መለስ ዜናዊ ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን አንዱ ናቸው። ወ/ሮ አዜብ አሁንም የህወሃት ኩባንያ የሆነውን ኢፍርትን በበላይነት እያስተዳደሩ የሚገኙ ሲሆን፣ በአዲስ አበባ በግላቸው ግዙፍ ህንጻዎች እያስገነቡ መሆኑን መሃንዲሶች ገልጸዋል ።
ኢህአዴግ እንደሚለው ሳይሆን፣ የአቶ መለስ ዜናዊ ቤተሰቦች በአዲስ አበባ ውስጥ ግዙፍ የሆነ የቢዝነስ ኢምፓየር ወይም ግዛት እየመሰረቱ ነው። ይህ በቪዲዮ ላይ የሚታዬው ህንጻ የአቶ መለስ እህት ጅምር ህንጻ ሲሆን፣ በመሃንዲሶች መረጃ መሰረት የህንጻው መሰረት ብቻ 24 ሚሊዮን ብር ወጥቶበታል።
በከተማዋ ውስጥ የሚገነቡት አብዛኛው ህንጻዎች ባለቤቶቹ የህወሃት ባላስልጣናት እና ከእነሱ ጋር ግንኙነት ያላቸው ሰዎች መሆናቸውን ምንጮች አክለው ይገልጻሉ። አስገራሚው ነገር፣ ሙስናን እንወጋለን የሚሉት የጸረ ሙስና ኮሚሽን ባለስልጣናት ሳይቀር በስማቸው እና በዘመዶቻቸው ስም ቤቶችን ገንብተው መገኘታቸው ነው።
ኢሳት በዚህ ዙሪያ ተጨማሪ ቪዲዮ ለወደፊቱ ያቀርባል።

No comments:

Post a Comment