Thursday, May 12, 2016

በአማራ ክልል ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ መዝነቡ ድርቁን ለመከላከል እንደማያግዝ ተነገረ፡፡

ግንቦት ፬ (አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በምስራቅ አማራ በድርቅ በተጎዱ አካባቢዎች ሰሞኑን በመጣል ላይ ያለው ዝናብ ተጠቅመው ልዩልዩ ዘሮችን ቢዘሩም ዝናቡ ወቅቱን ያልጠበቀ በመሆኑ ቡቃያው በሚፈልገው መጠን ፍሬ ሊያፈራ የሚችልበትን የዝናብ መጠን እያገኘ እንዳልሆነና የድርቅ አደጋውን ለመከላከል እንደማያግዛቸው ተጎጂ አርሶአደሮች ተናግረዋል፡፡

“ገበሬው ታታሪ ነው!” የሚሉት ተጎጂ አርሶአደሮች ዘንድሮ በድርቁ ከፍተኛ ውድመት እንደደረሰባቸው አውስተው ዓመቱን በስቃይ ለማሳለፍ መገደዳቸውንና ከሞትና ሽያጭ የተረፉትን እንስሶችን እነርሱ የሚመገቡትን ምግብ በመመገብ ህይወታቸውን ማቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡
“ዛሬ ግን ሁላችንም ድህነት ላይ ወድቀናል፡፡ ከብቱም ያለቀው አልቋል፡፡ተገቢው እርዳታም ባለመደረጉ ድጋሚ ለስደት ለመዳረግ ጫፍ ላይ ደርሰናል” ፣ “ድርቁን ለመከላከል የመስኖ ስራን እያስፋፋሁ ነው!” በማለት የገዢው መንግስት በተደጋጋሚ የሚናገረው ዜና ከእውነት የራቀ መሆኑን የሚናገሩት ተጎጂ አርሶአደሮች ከሃምሳ አባወራ ውስጥ ለስርዓቱ የተጠጉ ሶስትና አራት አመራሮች ብቻ ተጠቃሚ የሆኑበት አሰራር ብቻ እንዳለ አጋልጠዋል፡፡
አሁንም የገዥው መንግስት እርዳታውን በአግባቡ ካላቀረበላቸው ድጋሚ እንስሶችን በመሸጥ ህይወታቸውን ለማትረፍ እንደሚገደዱ ገልጸዋል፡፡
“ያሉን በሬዎች በመድከማቸው እንደ በፊቱ አርሰው ሊያበሉን አይችሉም” በማለት የሚናገሩት ሌላው የድርቅ ተጎጂ የእንስሶችን ነፍስ ለማትረፍ ከመጣር ውጭ ሰርተን የምግብ ፍጆታችን ለመሸፈን የምንችልበት ደረጃ ላይ አልደረስንም” በማለት የሚናገሩት አርሶ አደሩ “ጎልበታችን በሬዎች ናቸው” አሁን በዘነበው ዝናብ የታየው ቡቃያ እንስሶችን በመመገብ ህይወታቸውን ለመታደግ ከማገዝ ውጭ ድርቁን ለማስወገድ የሚያግዛቸው እንዳልሆነ ይገልጻሉ፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ በድርቅ ምክንያት ከመቶ በላይ የሰሜን ሸዋ አርሶ አደሮች ከመኖሪያ ቀያቸው ተሰደዋል።
በኢትዮጵያ የተከሰተው ርሃብ አድማሱን እያሰፋ ለአያሌ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ከአካባቢያቸው መፈናቀል ምክንያት እየሆነ ነው። በመዲናችን አዲስ አበባ ቀጭኔ መድሃኔዓለም ቤተክርስቲያን ጥጋት ስር ተከልለው የመከራ ሕይወት የሚመሩት ከሰሜን ሸዋ ደራ የመጡ ከመቶ በላይ አርሶ አደሮች ከነቤተሰቦቻቸው ለችግር ተዳርገዋል። ከመኖሪያ ቀያቸው የተፈናቀሉት ታዳጊ ሕጻናት ትምሕርታቸውን አቋርጠው ለጎዳና ተዳዳሪነት በመሆናቸው ወላጆቻቸው ላይ ከፍተኛ የሆነ ሥነልቦናዊ ጫና ፈጥሮባቸዋል።
የዘሩት ሳይበቅል ማሳው ላይ በመቅረቱ ለርሃብ በመጋለጣቸው ምክንያት ሕይወታቸውን ለማትረፍ ቀያቸውን ትተው የተሰደዱት አርሶ አደሮች በላስቲክ ቤት ውስጥ ተጠልለው ለዝናብና ለብርድ ተጋላጭ ሆነዋል። ተፈናቃዮቹ አርሶ አደሮች አሁንም በአዲስ አበባ ለተጨማሪ ስቃይ ተዳርገው ሕይወታቸውን በልመና መግፋት ግድ እንደሆነባቸው ተናግረዋል።
የሸገር ኤፍ ኤም ጋዜጠኛ ዮሐንስ የኋላወርቅ ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች ወደ ቀያቸው ተመልሰው አርሰው ለመብላት እንደሚፈልጉና መንግስት እገዛ እንዲያደርግላቸው ተማጽኖዋቸውን አሰምተዋል።
የገዥው መንግስት ባለስልጣናት ርሃቡን ሲደብቁ ቢከርሙም የኢትዮጵያ ርሃብ በዜጎች ላይ አሉታዊ ጫናውን ማሳረፉ ተባብሶ ቀጥሏል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ዓለም አቀፍ ግብረሰናይ ድርጅቶች ከሃያ ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያዊያን አፋጣኝ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው እየገለጹ ሲሆን አሁን ከተከሰተው የጎርፍ አደጋ ጋር ተዳምሮ ከፍተኛ የሆነ ሰብዓዊ ቀውስ በአገሪቱ ላይ ማንዣበቡን በጥናታዊ ሪፓርታቸው አመላክተዋል።

No comments:

Post a Comment