Monday, May 2, 2016

“የአማራ ክልል አስተማማኝ ሰላምና ጸጥታ አለበት” መባሉ ትዝብትን ፈጠረ፡፡

ሚያዚያ ፳፬(ሃያ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ብናልፍ አንዱ ዓለም ሰሞኑን የክልሉን ሰላም አስመልክተው እንደተናገሩት “በክልላችን በጣም አስተማማኝ ሰላም ያለበት ከጫፍ ጫፍ ድረስ ህብረተሰቡ ያለ ስጋት ወጥቶ የሚገባበት ምንም ዓይነት የጸጥታ ስጋት የሌለበት ክልል ነው” በማለት መናገራቸው በህዝቡ ዘንድ ትዝብት ፈጥሯል፡፡

በዚህ ዓመት በክልሉ የተለያዩ ቦታዎች የበርካታ ዜጎችን ሕይወት የቀጠፉ የእርስ በርስ ግጭቶች እንዲፈጠሩ ይሰራ እንደነበር የሚነገርለት የገዥው መንግስት “በጣም አስተማማኝ ሰላም አለ!” የሚል መግለጫ እንዲሰጥ ማድረጉ ከእውነት የራቀና የገዢው መንግስት ከህዝቡ ጋር የተለያየ፣ የህዝቡ ቁስል የማይሰማው መሆኑን የሚያሳይ ንግግር እንደሆነ ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
አቶ ብናልፍ በንግግራቸው በአለፉት ዓመታት በተለያዩ አካባቢዎች በስርቆት ፣የተለያዩ ሽፍቶች መንገድ ላይ ዘረፋ የሚካሄዱበት የሰው ህይወት የሚጠፋበት ፣በጸጥታ ችግር ህብረተሰቡ በስጋት ውስጥ የሚገባበት እንደነበር ገልጸው፤ በዚህ ዓመት ግን ይህን ከመሰረቱ የሚቀይር ስራ እንደተሰራ ሲናገሩ መደመጣቸው በህዝቡ ዘንድ ትልቅ ገረሜታን ፈጥሯል፡፡
“በያዝነው ዓመት ሰላማችን በትልቁ የተረጋገጠበት ሁሉም ዜጎች ያለ ስጋት የሚኖሩበት ክልል ማድረግ ተችሏል፡፡” የሚሉት አቶ ብናልፍ ይህ የተገኘው ሰላምም ያለፉት 25 ዓመታት ጥረት ውጤት መሆኑን ሲናገሩ ተሰምተዋል፡፡
የአቶ ብናልፍን ንግግር የሰሙ የክልሉ ነዋሪዎች ለሪፖርተሮቻችን በሰጡት አስተያየት “በዚህ ዓመት በክልሉ የነበረ አስተማማኝ ሰላም የለም!” በማለት የተከሰቱ ችግሮችን ሲዘረዝሩ “ሁሉም ዜጎች ያለስጋት የሚኖሩ በትክልል! ማለት ምን ማለት እንደሆነ አልገባንም” በማለት የከፍተኛ አመራሩ ንንግግር የሚቃወሙት አስተያየት ሰጪዎች “የጎንደር ህዝብ የክልሉ ዜጋ አይደለም ወይ? በወልቃይት የአማራነት ጥያቄ ምክንያት የተፈጠረው ግጭትና ደም መፋሰስን ለምን አርቀው ይመለከቱታል? በቅማንት ብሔረሰብና በአካባቢው ለዘመናት በአንድነት የኖሩት አማራዎች መካከል ሆነ ተብሎ በተፈጠረው አለመግባባት የተከሰተው ደም መፋሰስ የክልሉ አካል አይደለም ወይ?” በማለት በዚህ አመት የተከሰቱ ዋናዋና ችግሮችን ያነሳሉ፡፡
አስተያየት ሰጪዎቹ ከዚህ ባሻገር በጎንደር ወህኒቤት በተከሰተው የእሳት ቃጠሎ የጠፋው የሰው ሕይወት ፤በገዥው መንግስት ወታደሮችና በእስረኛ ቤተሰቦች መካከል የተከሰተው ግጭትና ደም መፋሰስ በዚህ ዓመት በክልሉ እንዳልተከሰቱ መቁጠር ፈጽሞ አግባብ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡
“የሃገራችን ሰላም እጅግ በጣም የተረጋጋና አስተማማኝ ሰላም ያለበት ነው፡፡ በዚህ ረገድ ከኛም አልፈን የጎረቤት ሃገራትን ሰላም ለማስጠበቅ የምንሰራ ህዝቦች ነን” በማለት በሃገራችን ስላለው ሰላም የሰጡት መግለጫ ‘የትኛዋን ሀገር’ የሚመለከት እንደሆነ ግራ የሚያጋባ መሆኑን የሚናገሩት አስተያየት ሰጪዎች “በቅርቡ በኦሮሚያ ህዝብ ተቃውሞ በቀረበበት የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን የፍትሃዊነት ጥያቄ ለወራቶች የተከሰተው ጥያቄና የገዢው መንግስት ወታደሮች የሰጡት የጥይት ምላሽ የበርካቶችን ህይወት የቀጠፈ ክንውን የተከሰተው በዚች በኛዋ ሃገር አይደለም ወይ?” በማለት ይጠይቃሉ፡፡
የአማራ ክልልን እወክላለሁ የሚለው ብአዴን/ኢህአዴግ አመራሮች በትግራይና አማራ ክልል ድንበሮች ላይ በየጊዜው የሚታየው አለመግባባትና የማንነት ጥያቄን አስመልክቶ በሚነሱ ግጭቶች ራሳቸውን በማግለል ታዛቢ መምሰላቸው እንደሚያሳዝን አስተያየታቸውን የሰጡ ነዋሪዎች እስካሁን በኃይል ቢታፈንም ምላሽ ያላገኘው የወልቃይት ማንነት ጥያቄ እና በተመሳሳይ በቅርቡ በእንቅስቃሴ ላይ ያለው የአላማጣና ኮረም ህብረተሰብ የማንነት ጥያቄም ምላሽ እንዲታፈን ከማድረግ አልፈው የክልሉ ሰላም አስተማማኝ ነው ማለታቸው ትዝብትን የሚፈጥር መሆኑን ለዘጋቢዎቻችን ተናግረዋል፡፡

No comments:

Post a Comment