Wednesday, September 9, 2015

ከዓመት በዓሉ ጋር ተያይዞ የሸቀጦች ዋጋ እየናረ ነው

ጷግሜን ፬ (አራት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለለስልጣን ሰሞኑን የአዲስ ኣመት በዓልን አስመልክቶ በሸቀጦች ላይ ዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀቱን ቢናገርም፣ የሸቀጦች ዋጋ ከንረት ሊታደገው አለመቻሉን ያነጋገርናቸው የአዲስአበባ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡

በአዲስአበባ በሳሪስና በሾላ ገበያዎች ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች እንደጠቆሙት ሰሞኑን የሸቀጦች ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡ በገበያዎቹ የአበሻ በመባል የሚታወቀው ሽንኩርት በኪሎ ከ17- 18 ብር፣ የፈረንጅ ሽንኩርት ከ21- 22 ብር በኪሎ በመሸጥ ላይ ነው፡፡ ከአንድ ሳምንት በፊት የሽንኩርት የአንድ ኪሎ ዋጋ ከ8 – 17 ብር የነበረ መሆኑ ሲታወስ የዋጋው ንረት ከፍተኛ መሆኑን መረዳት እንደሚቻል አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል፡፡
የምግብ ቅቤ በኪሎ ከ270- 290 ብር እየተሸጠ መሆኑን፣ የአንድ ዕንቁላል ዋጋ ከ3 ብር ከ75 ሳንቲም እስከ 3 ብር ከ85 ሳንቲም መናሩን ነዋሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡ የሌሎችም ሸቀጦች ዋጋ ንረት መታየቱንም አረጋግጠዋል፡፡
ባለፉት ወራት ከፍተኛ የዋጋ ንረት ያሳዩት የበርበሬና የምስር ምርቶችንም በተመለከተ መንግስት በተደጋጋሚ የአቅርቦት ችግር የለም ቢልም ዋጋቸው ግን አንዳችም መረጋጋት ማሳየት አልቻለም፡፡
የሥጋ ምርቶችንም በተመለከተ የበሬ ሥጋ በአማካይ በኪሎ ከ120 – 170 ብር በመሸጥ ላይ ሲሆን፣ የበግ ስጋ በኪሎ ከብር 90 – 140 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ በአንዳንድ የቁርጥ ሥጋ አቅራቢ ሉካንዳ ቤቶች የአንድ ኪሎ ሥጋ ዋጋ በአማካይ ከ200 – 250 ብር ነው፡፡ የሥጋ የችርቻሮ ዋጋ ካለፉት አንድ ወር ወዲህ የከብት አቅራቢዎች በደረሰኝ እንዲገበያዩ መገደዳቸውን ተከትሎ ዋጋው ቀስ በቀስ እየጨመረ መምጣቱን ነዋሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
የዶሮ ዋጋም በአማካይ ከ180 እስከ 300 ብር የሚሸጥ ሲሆን መካከለኛ በግ ከ1 ሺ 800 እስከ 2 ሺ 500 ብር ዋጋ እየተጠየቀበት ነው፡፡ የዶሮና የበግ ዋጋ በቀጣይ ሁለት ቀናት በከፍተኛ ሁኔታ ይጨምራል የሚል ሥጋት እንዳላቸው ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
የንግድ ውድድርና የሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ ኢኮኖሚያዊ መነሻ የሌላቸው የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ከሚመለከታቸው መ/ቤቶች የተውጣጣ ግብረሃይል መቋቋሙን በመግለጽ ነጋዴዎችን አስጠንቅቆአል፡፡
አንድ በዕንቁላል ንግድ ስራ ላይ የተሰማሩ ግለሰብ ስለባለስልጣኑ ማስጠንቀቂያ ተጠይቀው የዕንቁላል ዋጋ የናረው ከመኖ እጥረት ጋር በተያያዘ የአቅርቦት ማነስ በመከሰቱ ሲሆን፣ ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚረከቡበት ዋጋ ውድ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ መንግስት ዋጋ እንዳትጨምሩ ስላለ ብቻ ለመክሰር የምንነግድበት ሁኔታ ሊኖር አይችልም በማለት ማስጠንቀቂያውን አጣጥለውታል፡፡

No comments:

Post a Comment