Friday, September 18, 2015

የሲፒጄው ተወካይ የኢትዮጵያን ጋዜጠኞች አደነቁ

መስከረም ፮ (ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አለማቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተንከባካቢ ድርጅት፣ ሲፒጄ የምስራቅ አፍሪካ ተወካይ የሆኑት ቶም ሮድስ፣ የዞን 9 ጸሃፊዎች የዚህን አመት የአለማቀፍ የፕሬስ ነጻነት ሽልማት ማሸነፋቸውን ተከትሎ ለኢሳት እንደተናገሩት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ሽልማት የሚገባቸው በርካታ ጋዜጠኞች አሉ ሲሉ ጋዜጠኞች ለፕሬስ ነጻነት እየከፈሉ ያለውን መስዋትነት አወድሰዋል።

የዞን ዘጠኝ ጸሃፊዎችን ለመሸለም የፈለግነው በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን የፕሬስ አፈና ለአደባባይ በማብቃት ተጽኖ ለመፍጠር ነው ያሉት ቶም ሮድስ፣ ለዞን 9 ጸሃፊዎች የተሰጠው አለማቀፍ ትኩረት እንዲሁም በቅርቡ የተወሰኑ ጸሃፊዎች መፈታታቸው በእስር ላይ ያሉትን ሌሎች እስረኞች ትኩረት እንዲያገኙ ያደርጋቸዋል ብለዋል።
ጋዜጠኞችን በማሰር ኢትዮጵያ በአፍሪካ አንደኛ መሆኑዋን የጠቁሰት ቶም ሮድስ፣ ሽልማቱ የኢትዮጵያን ባለስልጣናት ስሜት ይቀይረዋል ተብሎ ብዙም ባይታመንበትም፣ ኢትዮጵያ ከውጭ መንግስታት ከፍተኛ የእርዳታ ገንዘብ የምታገኝ በመሆኑ፣ የአለማቀፉ ማህበረሰብ በኢትዮጵያ ላይ ትኩረት እንዲያደርግ ይረደዋል ብለዋል።
የተወሰኑ የዞን 9 ቡድን አባላትና ርእዮት አለሙን የመሰሉ ታዋቂ ጋዜጠኞች ሲፈቱ የፕሬስ ነጻነቱ ይሻሻላል ብለን ተስፋ ብናደርግም፣ የሰፉ ጌታቸውን የመሳሰሉ በሽብርተኝነት ተከሰው 7 አመት ሲፈረድባቸው ስናይ ደግሞ ሁኔታዎች እየተበላሹ መሄዳቸውን እናያለን ብለዋል። ብዙ ጋዜጠኞች በመታሰራቸውና አብዛኞቹም ከአገር በመልቀቃቸው ፣ ጠንካራ ድምጾችን የሚያሰሙ ጋዜጠኞች መጥፋታቸውንም ተወካዩ ገልጸዋል።
ሚ/ር ቶም ሮድስ ኢትዮጵያ በነበሩበት ወቅት ጋዜጠኛ ውበሸት ታዬንና ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን ለማግኘት ለማግኘት ሙከራ ቢያደርጉም እንዳልተሳካለቸው ተናግረዋል።

No comments:

Post a Comment