Tuesday, September 22, 2015

ረሃቡ የጠናባቸው ሰዎች ወደ ጎዳና እየወጡ ነው

መስከረም ፲፩ (አስራ አንድ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በደቡብ ክልል በጌዲዮ ዞን ከድርቅ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ረሃብ ተከትሎ በርካታ ዜጎች ወደ ከተማ እየፈለሱ ሲሆን፣ እርዳታ ማግኘት ባለመቻላቸው ጎዳና ላይ ማደር መጀመራቸውን የአካባቢው ምንጮች ገልጸዋል።

መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ያሰማሩዋቸው ባለሙያዎች በዞኑ 80 ሺ ህዝብ መራቡን ሪፖርት ሲያደርጉ፣ የዞኑ የመንግስት ባለስልጣናት በተቀራኒው በዞናቸው ምንም የተራበ ሰው የለም የሚል ሪፖርት አቅርበዋል።

ማንነታቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች በድብቅ በእዬ ቤቱ እየዞሩ በረሃብ ምክንያት ተኝተው ያገኙዋቸውን ሰዎች ፎቶ እያነሱ ለመንግስት ባለስልጣናት ማቅረባቸውን ተከትሎ፣ በድጋሜ ማጣራት እንዲደረግ ተብሎ መመሪያ ሲወርድላቸው፣ በዞናቸው 4 ሺ ሰዎች ብቻ በረሃብ መጠቃታቸውን ገልጸዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በባለስልጣናቱ በመበሳጨት ” የራሳችን ልጆች የሆኑት ባለስልጣናት እየበሉን ነው” በማለት ተቃውሞአቸውን እየገለጹ ነው።
በዋና ዋና ከተሞች በብዛት ህፃናትና ወጣቶች ጎዳና ላይ እየወጡ ሲሆን፣ የሚለምኑና የሚታመሙ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል። የስርቆት ወንጀልም ተበራክቷል።
በሌላ በኩል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዛሬ ባወጣው መግለጫ በኢትዮጵያ የምግብ እርዳታ የሚፈልገው ህዝብ ቁጥር ባለፈው ታህሳስ ወር ከተገለጸው አሃዝ መብለጡን አስታውቋል። ቀድም ብሎ 4 ሚሊዮን 500 ሺ ህዝብ የምግብ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ድርጅቱ የገለጸ ቢሆንም፣ ተጨማሪ 400 ሺ ህዝብ የምግብ እርዳታ እየተደረገለት ነው ብሎአል። በተለያዩ ክልሎች ረሃቡ እየተባባሰ በመምጣቱ አፋጣኝ መልስ እንደሚያሻ ድርጅቱ አስታውቋል።

No comments:

Post a Comment