Thursday, September 10, 2015

የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የክልሉን ትራንስፖርት ባለስልጣን ቢሮ ሁከትፈጣሪ በማለት ውሳኔ አሳለፈ፡፡

ጷግሜን ፭ (አምስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ቢሮው በጣና ሐይቅ ላይ በቱሪስት ማስጎበኘት ስራ በተሰማሩ ማህበራት አሰራር ጣልቃ በመግባቱ በተከሰሰበት የጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ አስተላልፎበታል፡፡

ባለስልጣን ቢሮው የቱሪስት ጀልባዎችን በተራ ለማሰራት ያደረገው የተራ ማስከበር ስራ ህግና ደንቡን ያልተከተለ ነው በማለት የተቃወመውን የጥዋት ብርሃን አነስተኛና መለስተኛ የግል ጀልባ ባለንብረቶች ማህበር ፣ ያልኩትን አልፈጸማችሁም በማለት አስራ አምስት ጀልባዎችን ከየካቲት 25/2007 እሰከ ሰኔ 12/2007 በካቦ ገመድ በማሰር ምንም እንቅስቃሴ እንዳያደርጉ በማድረጉ የባለስልጣኑ መስሪያ ቤቱ የተቋቋመበትን አዋጅ የጣሰ እና በደንብ ቁጥር 118/2005 በባህር ትራንስፖርት መመሪያውና በቱሪዝም አዋጅ ቁጥር 80/2005 ላይ የተደነገጉትን የኦፕሬተሮች ፈቃድ የምስክር ወረቀት የተጠቀሱትን ድንጋጌዎችን የጣሰ አሰራር በመሆኑ ችሎቱ ቃል በቃል ‹‹ የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ትራንስፖርት ባለስልጣን ቢሮ ሁከት ፈጥሯል ፡፡ሁከቱንም ያቁም ! ›› የሚል ግሳጼ አዘል ውሳኔ መስጠቱን ከስፍራው የደረሰን ዜና አመላክቷል፡፡
‹‹ ጀልባዎች በባለስልጣኑ ቢሮ ለ 112 ቀናት በመታሰራቸው ከ 320 በላይ የሆኑ የማህበሩ አባላትና ቤተሰቦችን በረሃብ ቀጥቷል ›› የሚለው የጥዋት ብርሃን አነስተኛና መለስተኛ የግል ጀልባ ባለንብረቶች ማህበር ፣ ተፈጸመብኝ ያለውን ወንጀልና የተፈጠረውን የመልካም አስተዳደር ችግር በህግ አደባባይ በመታገል ውሳኔ ቢያገኝም ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ለህግ ተገዥ መሆኑን እንደ ሽንፈት በመቁጠር የማህበራቸውን እንቅስቃሴ ለማስቆም የሚያደርገውን እንቅስቃሴ እንዲያቆም የሚጠይቅ ደብዳቤ ለ18 የክልልና 4 የፌደራል መንግስት መስሪያ ቤቶችና የሚዲያ ተቋማት ባሰራጨው ደብዳቤ አስታውቋል፡፡
ማህበሩ በደብዳቤው ይህንን ዓይነት የመልካም አስተዳደር ህፀጽ በህገ መንግስቱና ሌሎች የሃገሪቱ ደንቦችን መሰረት አድርጎ የሚታገለው አስተሳሰብ መሆኑን ለሚመለከተው ሁሉ አረጋግጧል፡፡
ትራንስፖርት ቢሮው የሃገሪቱን የንግድ ፖሊሲ ምሰሶ የሆነውን የነጻ ገበያ የውድድር መርህን በመጣስ የቱሪስት ጀልባዎች ከውድድር ይልቅ በተራ እንዲሰሩ በማስገደድ የአንድ ወገንን ጥቅም ለማስከበር የሚያደርገው አሰራር የጠባቂነት አስተሳሰብ እንዲሰፍን እና በጣና ሐይቅ ላይ ከሚሰሩ አቻ ማህበራት ጋር ጠብ ፣ረብሻና ትርምስ እንዲፈጠር አነሳስቷል በማለት ቅሬታውን የሚያቀርበው ማህበር፣ አሁንም ከፍርድ ቤቱ ውሳኔ በኋላ ማህበሩን የሚጻረሩ ደብዳቤዎችን ማሰራጨቱ ህገወጥ ነው በማለት የማህበሩ አባላት ተቃውመዋል፡፡
ባለስልጣን ቢሮው ለሚፈጽምባቸው የስም ማጥፋት ወንጀል በህግ አግባብ ለመጠየቅ እየተዘጋጁ መሆኑን የሚናገሩት የማህበሩ አባላት ማህበሩ በህጋዊ መንገድ የራሱን ስራ አፈጻጸም የደንበኞችን እና መርሃ ግብር ለሚመለከተው የመንግስት አካል በአዋጁ መሰረት ሪፖርት እያደረገ የሚሰራ ህጋዊ ማህበር መሆኑን ገልጿል፡፡ማህበሩ ህጋዊ የወደብ ቦታ ከጣና ሐይቅ ትራንስፖርት ድርጅት ተከራይቶ በህጋዊ መንገድ እያስተናገደ መሆኑን አስታውቓል።
የባለስልጣኑ ቢሮ የተለመደ ጅምላ ውንጀላውንና ድህነትን ለማንበረከክ የሚያደርጉትን ጉዞ ለማደናቀፍ ህጋዊውንና ህገወጡን የአሰራር ስርዓት በማጣቀስ አንገገታቸውን ለማሰደፋት የሚያደርገውን አፍራሽ አሰራር እንዲያቆም ወጣቶቹ ጠይቀዋል፡፡
የትራንስፖርት ባለስልጣኑ ቢሮ ኃላፊ አቶ መጋቢያው ጣሰው በተለያየ ጊዜያት የሚጽፉት ደብዳቤ መመሪያና ደንቡን ያልተከለ፣ አምባ ገነናዊ የአጻጻፍ ዘየን የተከተለ ከመሆኑም በላይ የሰበር ሰሚ ችሎቱን በቢሮው ላይ ወሳኔ ሲያሳልፍ ‹‹ አልፈጽምም !! ›› በማለት አምባገነናዊ ምላሽ በመስጠት ሲቃወሙ እንደነበር በቦታው ተገኝተው የፍርድ ሂደቱን የተከታተሉ እማኞች ገልጸዋል፡፡
ማህበሩ አክሎ የትራንስፖርት ባለስልጣን ቢሮው የማህበሩን ጀልባዎችን ያለአግባብ ለ 112 ቀናት በማሰር ገቢያቸው እንዲቋረጥ ያደረገበትን ከ አንድ ሚሊዮን ብር በላይ ክሳራ ለአባላቱ እንዲከፍል የፍትሃ ብሔር ክስ ላይ እንደሆነ ከፍርድ ቤት የሚወጡ መረጃዎች አመላክተዋል፡፡
በሌላ በኩል በባህርዳር የአርበኞች ግንቦት7 አባላት በሌሊት በራሪ ወረቀቶች በትነዋል። ውሸት ሰልችቶናል፣ ወጣቱ ትውልድ ከአርበኞች ግንቦት7 ጋር በመሆን አገሩን ነጻ ያውጣ የሚሉ በራሪ ወረቀቶች በየመንገዱ ላይ ተበትነውና በተለያዩ ዛፎችና ምሰሶዎች ላይ ተለጥፈው ታይተዋል።

No comments:

Post a Comment