Tuesday, September 15, 2015

የአፋር ክልል ባለስልጣናት መስማማት አልቻሉም

መስከረም ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በቀድሞው የህወሃት አባልና በሁዋላም የአፋር ፓርቲ መስርተው የክልሉ ፕሬዚዳንት ሆነው ለ20 አመታት በስልጣን ላይ የነበሩት አቶ እስማኤል አሊ ሴሮ ከስልጣናቸው ከተነሱ በሁዋላ፣ የአብዴፓ ሊቀመንበር ሆነው በተመረጡት በአቶ ጠሃ ሙሃመድ ቡድንና በአቶ አሊ ሴሮ ቡድን መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ከፍተኛ ደረጃ ደርሷል። የውዝግቡ መነሻ አቶ ጠፋ የክልሉ ፕሬዚዳንት ሊሆኑ አይገባም በማለት የአቶ አሊ ሴሮ ደጋፊዎች ተቃውሞ ማስነሳት በመጀመራቸው ነው።

ክልሉ በጊዜያዊ መስተዳድሩ በአቶ አወል አርባ ለ3 ወራት ያክል እየተመራ እንዲቆይ ውሳኔ ተላልፏል። ክልሉን በበላይነት የሚያስተዳድረው ህወሃት የሽምግልና ጥረት ቢጀምርም አልተሳካለትም።
ባለፈው ሚያዚያ ወር ላይ ኢሳት በክልሉ ፕሬዚዳንት እስማኤል አሊ ሴሮና በጸጥታ ዘርፍ ሃላፊውና በፍትህ ቢሮ ሃላፊው መካከል የከረረ ጠብ መነሳቱን ጠቅሶ፣ አቶ እስማኤል ለ24 አመት የያዙትን የፕሬዚዳንትነት ቦታ እንደሚለቁ ፍንጮች መታየታቸው አሁን ለታየው የስልጣን ሽኩቻ መንስኤ መሆኑን፣ አቶ አሊ ሴሮ ለእርሳቸው ቀረቤታ ያላቸውንና አሁን ጊዜያዊ ፕሬዚዳንት የሆኑትን አቶ አወል አርባን በፕሬዚዳንትነት ማስመረጥ እንደሚፈልጉ ፣ የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊው አቶ ስዩም አወል ደግሞ የራሳቸውን ታማኝ ሰው ለማስመረጥ እንደሚፈልጉ ዘግቦ ነበር።
አቶ እስማኤል ባለፉት 24 አመታት ለፈጸሙዋቸው ከባድ ወንጀሎች ተጠያቂ እንዳይሆኑ የራሳቸውን ሰው ለማስመረጥ መፈለጋቸውን የአፋር ሰብአዊ መብቶች ድርጅት ሊ/መንበር አቶ ገአስ አህመድ በወቅቱ ገልጸው ነበር።

No comments:

Post a Comment