Friday, September 25, 2015

አቡነ ጴጥሮስ ወደ ቦታቸው ይመለሱ!

የጀግንነት ፣ የአማኝነት ፣ የአይደፈሬነት ፣ የእውነት ፣ የኢትዮጵያዊነት ተምሳሌት የሆኑት አቡነ ጴጥሮስ ወደ ቦታቸው ይመለሱ ፡፡ አገራቸውን በእብሪት ሊወር የመጣን ፋሽስት ንጉስን ተከትለው ማይጨው በመውረድ በጦር ሜዳ የተፋለሙ ከሽንፈት ማግስት ንጉስኑና ጋሻ ጃግሬዎቻቸው እግሬ አውጭኝ ብለው ሲፈተለኩ ወደ ደብረ ሊባኖስ በመውረድ በፆም ፣ በጸሎት ብሎም ሕዝቡን በማስተማርና አርበኞችን በማበረታታት የወራሪውን ድብቅ ሴራ ያጋለጡ መንፈሳዊ አባት ነበሩ ፡፡ ታዲያ ሕዝባዊ ቅቡልነታቸውን ያየው ወራሪው ፍሽስት አርበኞችን አውግዘው የኢጣሊያብ ወራሪነት ቢቀበሉ የተደላደለ ኑሮ እንደሚገጥማቸው ሲያረዳቸው “በመርዝ ጋዝ እና በጦር መሳሪያዎቻችሁ በሕዝቤ ላይ የፈጸማችሁት ፍጅት እና ዋይታ ያቀረባችሁትን ጥያቄ ህሌናየ እንዳይቀበል ያግደዋል ፤ ይሄንን ወንጀላችሁን ካላወገዝኩስ እንዴት ብየ ፈጣሪ ፊት እቆማለሁ?” በማለት ጥያቄያቸውን ያጠጣሉ በገዳዮቻቸው ፊት ቆመውም “የአገሬ ሕዝብ ሆይ ለወራሪው ጣሊያን አትገዛ ፤ ፋሽስቶች አርበኞች ባንዳ ናቸው የሚሏችሁን አትመኗቸው ፤ አርበኞች አገራቸውን ከወራሪዎች ነፃ ለማውጣት የሚታገሉ ጀግኖች ናቸው ፤ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿ የወራሪውን ሕግ አይቀበሉም ፡ ይሄንን ወረራ የተቀበለን ሰው ገዝቸዋለሁ” በማለት በገዳዮቻቸው ፊት ሞትን በክብር የተቀበሉ አባት ናቸው (የዛሬ አባቶችስ?)

ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ስለመለስ በአዲስ አበባ የቀላል ባቡር ግንባታ ምክንያት የአቡኑ የመታሰቢያ ኃውልት በተነሳበት ወቅት የደረሰውን ተቃውሞ ተቃውሜዋለሁ (የተወረርነው ድሆች ስለነበርን ነውና!) መንግስትም በወቅቱ ግንባታው እንዳለቀ የአቡኑ ኃውልት ቀድሞ ከነበረው ባማረ መልኩ ወደ ቦታቸው እንደሚመለስ ማብሰሩ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው ፡፡ አሁን ባቡሩ ተጠናቆ ስራ ጀምሯል ፡፡ እናም አቡነ ጴጥሮስ ወደ ቦታቸው (የሞት ሽልማት ወደ ተቀበሉባት የመታሰቢያ ስፍራቸው) በክብር ይመለሱ ፡፡ ጀግኖችን ካላከበርንና ካላወደስን ነገ ይች አገር በሁሉም መስክ የምትፈልጋቸውን ጀግኖች ማፍራት አንችልምና!!!
Getnet Almaw Tiruneh's photo.

No comments:

Post a Comment