Tuesday, January 2, 2018

ህወሃትን ለመቆጣጠር የሚደረገው ትንቅንቅን እንደቀጠለ ነው

ህወሃት ከወር በላይ ለፈጀ ጊዜ ግምገማ በማድረግ የአመራር ለውጥ እንዳደረገ ቢናገርም፣ በድርጅቱ ውስጥ ያለው ሽኩቻ አሁንም እንደቀጠለ ነው። የህወሃት ማዕከል ሆኖ ለመውጣት ሶስት ሃይሎች በዋናነት እየተፋለሙ መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ። የደህነንቱ ሹም አቶ ጌታቸው አሰፋ በአቶ ስብሃት ነጋ ታግዞ የወ/ሮ አዜብንና የአቶ አባይ ወልዱን ጥምረት ለመስበር ቢችልም፣ በጄ/ል ሳሞራ የኑስ በኩል የተፈጠረውን ሰንሰለት መስበር አልቻለም። አቶ ጌታቸው አሰፋ በቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት እና በአቶ ወልደስላሴ ወልደሚካኤል ሴራ ከአቶ መለስ ዜናዊ ጋር በመጋጨቱ ስልጣኑን ለማጣት ጫፍ ደርሶ በነበረበት ወቅት፣ አቦይ ስብሃት መለስን አሳምነው ለተወሰነ ጊዜ በስልጣን ላይ እንዲቆይ አድርገውት የነበረ ሲሆን፣ የአቶ መለስ ድንገተኛ ህልፈት ለወ/ሮ አዜብ፣ ለአባይ ወልዱና በእነሱ ዙሪያ ተሰልፈው ለነበሩ ሃይሎች ሁሉ መርዶ ይዘ ሲመጣ ለአቶ ጌታቸው ግን የደስታ ብስራት እንደነበረ ምንጮች ይገልጻሉ። አባይ ወልዱ ወደ ስልጣን ከመጣበት ቀን ጀምሮ ብቸኛ ደጋፊው አቶ መለስ ዜናዊ
የነበሩ ሲሆን፣ በዚህ ውለታም ከወ/ሮ አዜብ ጋር እስከመጨረሻው ለመቆምና የአቶ ጌታቸውን ሃይል ለመስበር ሙከራ ሲያደርግ ቆይቷል። አቶ ጌታቸው ጊዜ ጠብቆ በወ/ሮ አዜብ ላይ የበቀል በትሩን በማሳረፍ የሀወሃት ቁልፍ ሰው በመሆን መለስን ለመተከታት እየሞከረ ቢሆንም፣ የጄ/ል ሳሞራን የደህንነት መዋቅር ለመስበር ባለመቻሉ፣ ቀሪው ፍልሚያ በሁለቱ ሃይሎች መካከል መሆኑን ምንጮች ይገልጻሉ። አቶ ጌታቸው በአሁኑ የውስጥ ትግል አቶ ስብሃትን ከፊት ለማሰለፍና ቁልፍ ሰው አድርጎ ለማሳየት የፈለገው በቆዬ ውለታና አቶ ስብሃት በድርጅቱ ውስጥ ባላቸው አክብሮት መሆኑን የሚገልጹት ምንጮች፣ አቶ ስብሃትም አጋጣሚውን ተጠቅመው የበቀል ጅራፋቸውን በወ/ሮ አዜብ ላይ ማዞራቸውን ይገልጻሉ።
ጄ/ል ሳሞራ ከመለስ ሞት በሁዋላ አገሪቱ ሳትፈራርስ እንድትቀጥል ያደረገው የፖለቲካ አመራሩ ሳይሆን የመከላከያው የአመራር ጥንካሬ ነው በማለት ራሱን የህወሃት ቁልፍ ሰው አድርጎ ለማውጣት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆን፣ ከድህንነት መዋቅሩ ጋር እየተላተመ ነው። የደህንነት መዋቅሩና መከላከያው ዋነኞቹ የስልጣን ተፋላሚዎች እየሆኑ ሲሆን፣ ውዝግባቸው እንደሚቀጥልና በአጭር ጊዜ መልስ ያገኛል ተብሎ እንደማይጠበቅ ምንጮች ይናገራሉ።
የሁለቱ ሃይሎች ፍጥጫ ለድርጅቱ እና ለአመራሩ ህልውና ስጋት በመፈጥሩ ለጊዜው ከሁለቱም ወገን አይደለም የተባለውን ዶ/ር ደብረጺዮንን ከብረሚካኤልን በሊቀመንበርነት ለማስቀመጥ ውሳኔ የተላለፈ ቢሆንም፣ ዶ/ር ደብረጺዮን በድርጅቱ ውስጥ ማእከል ሆኖ ለመውጣት አቅም የሚያንሰው ሰው በመሆኑ፣ የሁለቱ ሃይሎች ሽኩቻ ከደ/ር ደብረጺዮን ጀርባ እንደሚካሄድ ይገልጻሉ፡፡

No comments:

Post a Comment