Tuesday, January 23, 2018

የፓለቲካና የሕሊና እስረኞች ካለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱና ጥፋተኞቹም በህግ እንዲጠየቁ ሲል ለኮንሶ ሕዝብ መብት የሚታገሉ ሃይሎች ገለጹ

ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጡ የኮንሶ ሕዝብ የሰብዓዊ መብት ታጋዮች ኅብረት በህወሃት ኢህአዴግ አገዛዝ ካለጥፋታቸው ተወንጅለው በእስር የሚማቅቁ የፓለቲካና የሕሊና እስረኞች ካለምንም ቅድመ ሁኔታዎች እንዲለቀቁ ጠይቋል።
ከህግ አግባብ ውጪ በዜጎች ላይ እስራትና ግድያ ጨምሮ የተለያዩ የመብት ጥሰቶችን የፈጸሙ የስርዓቱ ባለስልጣናትና ትእዛዙን ተቀብለው ወንጀሉን የፈጸሙ ግለሰቦችና ተቋማት ተለይተው በህግ ሊጠየቁ ይገባል። ወንጀለኞቹ ተለይተው ጉዳያቸው በገለልተኛ አጣሪ አካል ተመርምሮ ሕጋዊ እርምጃ ሊወሰድባቸው ሲል ታጋዮቹ አሳስቧል። 

ስርዓቱ ሁሉንም እስረኞች ለመልቀቅ የገባውን ቃል በማጠፍ 52 የአካባቢው ተወላጆች ብቻ ክሳቸው ተቋርጦ በይቅርታ ስም እንዲፈቱ በማድረግ ትግሉን ለማዳከም አገዛዙ የሚያደርገው ሙከራ እንደማይሳካም ገልጸዋል። የኮሚቴ አባላትን ጨምሮ፣ ምሁራን፣ ነጋዴዎች፣ አርሶ አደሮች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የባህልና የሃይማኖት አባቶች በአጠቃላይ ቁጥራቸው ከ400 በላይ ሰላማዊ ዜጎች አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ ብሎአል። ይህም አገዛዙ ለሕዝብ ያለውን ንቀትና ጥላቻ ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል ብሏል መግለጫው።
የኮንሶ ተወላጆች ከተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በጋራ በመሆን ይህን አምባገነን ስርዓት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በመጣል ሁሉንም ያሳተፈ ስርዓት እስኪፈጠርና የወያኔ ግብአተመሬት እስኪፈጸም ትግላቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።
ባለፈው ሳምንት አገዛዙ በኮንሶ ግጭት ምክንያት ከታሰሩት ውስጥ 52 ሰዎች ክሳቸው ተቇርጦ በምህረት ወይም በይቅርታ እንደምፈቱ ቢገልጽም፣ የተፈቱት ሰዎች አንዳንዶቹ የተፈረደባቸውን ጊዜ የጨረሱ ሲሆን፣ ሌሎቹ ደግሞ የተፈቱት በይቅርታ ወይም በምህረት ሳይሆን በዋስ ነው። አንዳንዶቹ ከፍተኛ የሆነ ገንዘብ እየተጠየቁ እንደሆነም ከቤተሰቦቻቸው ለማወቅ ተችሎአል። አሁንም ድረስ ሰዎች እየታሰሩ መሆኑን ከአካባቢው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

No comments:

Post a Comment