Tuesday, January 2, 2018

በአርበኞች ግንቦት7 ስም በተከሰሱት ላይ እስከ 16 ዓመት የሚደርስ እስራት ተፈረደ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ጌታሁን በየነ ክስ መዝገብ በተከሰሱት 9 ግለሰቦች ላይ እስከ 16 ዓመት የሚደርስ ፍርድ አስተላልፏልል። 1ኛ ተከሳሽ ጌታሁን በየነ 9ኛ አመት ፣ 2ኛ ተከሳሽ ዶ/ር አስናቀ አባይነህ እና 5ኛ ተከሳሽ አለማየሁ ንጉሴ 16 አመት ከ6ወር፣ 4ኛ ተከሳሽ ብራዚል እንግዳ 15 አመት ተፈርዶባቸዋል። 
7ኛ ተከሳሽ ያምላክነህ ገዛኸኝ፣ 8ኛ ተከሳሽ አብዱ ሙሳ እና 14ኛ ተከሳሽ ደመላሽ ቦጋለ ደግሞ እያንዳንዳቸው በ5 አመት፣ 12ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ፍቅሬ እሸቱ 4 አመት ከአራት ወር እንዲሁም 13ኛ ተከሳሽ ባንተወሰን አበበ 3አመት ከ10 ወር ተፈርዶባቸዋል።
ተከሳሾቹ የተላለፈባቸውን ውሳኔ እንደሰሙ "የታገልነው የህይወት መስዋዕትነት ለመክፈል ነው፣ እናንተ ዳኞች ከእነ ሳሞራና አባይ ፀኃዬ በላይ ትጠየቃላችሁ፣ ወያኔ አንድ አመት አይቆይም፣ የጫካ ውላችሁ አይሳካም፣ እኛ የታገልነው ለመቶ ሚሊዮን ህዝብ ነው፣ ህወሓት ይቀበራል፣ነፃ እንወጣለን፣ ከግንቦት7 ጋር ወደፊት ግንቦት7 ያሸንፋል " ሲሉ ተናግረዋል። 


በሌላ በኩል ደግሞ እነ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ የቂሊንጦ እስር ቤት ኃላፊን በዘር ማጥፋት ወንጀል እንደሚጠይቋቸው ተናግረዋል።
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በተከሳሾቹ ላይ የዐቃቤ ሕግ 83ኛ ምስክር ሆነው የቀረቡት የቂሊንጦ እስር ቤት ደህንነትና ጥበቃ ኃላፊ ዋና ኦፊሰር ገብረማርያም ወልዳይ ኣብርሃ ሊመሰክሩ በቀረቡበት ወቅት ከእስረኞቹ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል።
ዋና ኦፊሰር ገብረማርያም በቂሊንጦ ቃጠሎ ወቅት እስረኞችን በመግደልና በማስገደል እንዲሁም አስከሬናቸውን በእሳት በማቃጠል ተጠያቂ ናቸው ሲሉ ተከሳሾች ተናግረዋል። 1ኛ ተከሳሽ መቶ አለቃ ማስረሻ ሰጤ ምስክር ሆነው የቀረቡትን ዋና ኦፊሰር ገብረማርያም ወልዳይ በዘር ማጥፋት ወንጀል የሚጠይቋቸው በመሆኑ መመስከር እንደሌለባቸው ገልፆአል። 5ኛ ተከሳሽ አግባው ሰጠኝ ምስክሩ በቂሊንጦ ቃጠሎ ወቅት ሰው ገድለው እሳት ውስጥ በመጨመር ወንጀል እንደፈፀሙ ለችሎቱ ተናግሯል። 4ኛ ተከሳሽ አበበ ኡርጌሳ ደግሞ ምስክሩ ለችሎቱ ጠቁመው ባሳዩት ወቅት "ያውቀኛል። ሲገድልና ሲያስገድል የነበረ ሰው ነው። በዘር ማጥፋት ሊጠየቅ የሚገባው ሰው ነው" ብሏል። 33ኛ ተከሳሽ ሸምሱ ሰኢድ "ገድሎ ማዕረግ የተሰጠው፣ ዞን 5 የተባለ የድሃ ልጅ የሚሰቃይበት እስር ቤት ያሰራ ሰው ነው።" ሲል ዋና ኦፊሰሩ እንዳይመሰክሩ ተቃውሟል። በተጨማሪም 31ኛ ተከሳሽ ጌታቸር እሸቴ "ምስክሩ ህሊናቸውን የሸጡ ናቸው። እንደሳቸው ህሊናቸውን የሸጡ አሉ። መንግስት ጨፍጭፌያለሁ ብሎ ይቅርታ ከጠየቀ በኋላ እንኳን ከስህተታቸው አልተማሩም" ሲል ተቃውሞውን ገልጿል።
ተከሳሾቹ ዋና ኦፊሰር ገብረማርያም ወልዳይ እንዳይመሰክሩባቸው ተቃውሞ ካሰሙ በኋላ፣ 18ኛ ተከሳሽ አንጋው ተገኘ "እኛ ፍትህ እናገኛለን ብለን ሳይሆን ለታሪክ እንዲመዘገብ ስለምንፈልግ ይመስክር" ብሏል። ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ ዋና ኦፊሰር ገብረማርያም ወልዳይ እንዲመሰክሩ ተከሳሾቹን ካግባቡ በኋላ ተከሳሾች ምስክርነቱ እንዲቀጥል ተስማምተዋል።

No comments:

Post a Comment