Wednesday, January 31, 2018

በሰሜን ወሎ እየተካሄደ ያለውን የስራ ማቆም አድማ ተከትሎ ከ200 በላይ ሰዎች ታሰሩ

በወልድያ፣ መርሳ፣ ስሪንቃና ቆቦ ከተሞች በመካሄድ ላይ ያለውን የስራ ማቆም አድማ ተከትሎ ከትናንት ጀምሮ ከ200 በላይ ዜጎች ታስረዋል። ከታሰሩት መካከል የመንግስት ሰራተኞች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ነጋዴዎችና ወጣቶች ይገኙበታል። በርካታ ወጣቶች ከተያዙ በሁዋላ ወዳልታወቀ ስፍራ ተወስደዋል። ከፍተኛ የእስር ዘመቻ እየተካሄድ ያለው ወልድያ ላይ ነው። ቀደም ሲል የክልሉ ፕሬዚዳንት ገዱ አንዳርጋቸው የሚታሰር ሰው እንደማይኖር ቃል ገብተው የነበረ ቢሆንም፣ ቃላቸው ሳይጠበቅ በስብሰባ ላይ የተሳተፉ ምክሮችን የለገሱ ሰዎች ሳይቀሩ እየታሰሩ ነው። 
ምንም እንኳ አሁንም ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት በአካባቢው ተሰማርቶ የሚገኝ ቢሆንም፣ ህዝቡ ግን ዛሬም የስራ ማቆም አድማውን ቀጥሎ ውሎአል። ሆቴሎች፣ ሱቆችና ሌሎች አገልግሎት ሰጪ መስሪያ ቤቶችና ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል። ከወልደያ እስከ ቆቦ ያለው መንገድ እንደተዘጋ ሲሆን፣ ወታደሮች መንገዶችን ለማስከፈት ሙከራ አላደረጉም። 

የአካባቢው ተወላጅ የሆነው አለምነው መኮንንና የፌደሬሽን ምክር ቤት አባሉ ያለው አባተ ወደ አካባቢው በመንቀሳቀስ ህዝቡ ተቃውሞውን እንዲያቆም ለማግባባት ቢሞክሩም ፣ ህዝቡ ሳይቀበላቸው በመቅረቱ አካባቢውን ለቀው ወጥተዋል። የህዝቡ እምቢተኝነት ያበሳጫቸው የአገዛዙ ባለስልጣናት ወታደሮችን በሌሊት እየላኩ ወጣቶችን እያፈሱ ነው።
የአማራ ክልል ኮሚኒኬሽን ቢሮ ዛሬ ባወጣው መግለጫ የእስር ዘመቻው መቀጠሉን አስታውቋል። በሰሜን ወሎ የሚደረገው ህዝባዊ የለውጥ እንቅስቃሴ በዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር እጦት የተነሳ መሆኑን የክልሉ መግለጫ ቢጠቅስም፣ ጥያቄውን ለማቅረብ የተሄደበት መንገድ ትክክል አልነበረም በማለት አውግዞታል። የአማራ ክልል መግለጫ በርካታ ወጣቶችን ማበሳጨቱን ወጣቶች ለኢሳት ተናግረዋል።
በሌላ በኩል ደግሞ የመርሳ ወጣቶች በራሳቸው ተነሳሽነት ዛሬ ከተማቸውን ሲያጸዱ ውለዋል። ከአማራ ክልል ወደ ትግራይ የሚወስደው ዋናው መንገድ እንደተዘጋ በመሆኑ፣ የተሽከርካሪና በሰሜን ወሎና በትግራይ ክልል መካከል የሚደረገው የንግድ ግንኙነት ተቋርጧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሰሜን ወሎ የተነሳውን ተቃውሞና የተወሰደውን የሃይል እርምጃ በመቃወም የአማራ ክልል ልማት፣ ቤቶችና ኮንስትራክሽን ቢሮ የ2010 በጀት ዓመት የመጀመሪያ መንፈቅ አመት የእቅድ ግምገማ ስብሰባ ጥር 17 ቀን 2010ዓም በተደረገበት ወቅት አብዛኞቹ ሰራተኞች ሳይገኙ ቀርተዋል።
የተቋሙ ሠራተኞች በወገኑ እልቂትና ጉዳት ከልብ በማዘን ከሥራ በፊት ሰላም ይቅደም በሚል መርህ አንሰበሰብም ማለታቸው ታውቋል። በ ወ/ሮ ገነት ገ/እግዚአብሔር የሚመራው መስሪያ ቤት ቀኑን ሙሉ የተገኙና በከፊል የተገኙ ሰራተኞች ስም ዝርዝር እንዲላክ የሚያሳስብ ደብዳቤ መጻፋቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
የአጋዚ ወታደሮችና የፌደራል ፖሊሶች በወልድያ፣ መርሳና ቆቦ በርካታ ወጣቶችን በአሰቃቂ ሁኔታ መግደላቸው ይታወቃል።

No comments:

Post a Comment