Monday, January 29, 2018

በሕወሃት አገዛዝ በቅርቡ በአሜሪካ የኢሕአዴግ አምባሳደር ሆነው የተሾሙት አቶ ካሳ ተክለብርሃን በቴሌ ኮንፈረስ ሲያካሂዱት የነበረው ውይይት በሕዝብ ተቃውሞ ተቋረጠ።

በአሜሪካ ከ11 ከተሞች የተውጣጡ ኢትዮጵያውያን ተመርጠው ከአምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን ጋር በስልክ ኮንፈረንስ ለመወያየት ታቅዶ ራሳቸውን ካስተዋወቁ በኋላ በጥያቄና መልስ ጊዜው ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል። አቶ ካሳ ስለህዳሴና ልማት እንዲሁም ኢትዮጵያን ለውጠናል ሲሉ የስልክ ውይይት ተሳታፊዎቹ ግን መጀመሪያ ሕዝብን መግደል አቁሙ ሲሉ አምባሳደሩን አውግዘዋል። በአሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ በሕወሃት የተሾሙት አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን ስራ ከጀመሩ አንድ ወር ተኩል ሳይሆናቸው ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል። ገና ከመሾማቸው በተቃውሞ ላይ ያለውን ዲያስፖራ የመለወጥ አቅሙ አለኝ በማለት ሲኩራሩ እንደነበር ይነገራል። በሚኒሶታ የተመረጡ የሶማሌ ኢትዮጵያ ተወላጆችን በማነጋገር ከዲያስፖራው ጋር በአደባባይ መታየት የጀመሩት አቶ ካሳ ተክለብርሃን ትላንት በቴሌ ኮንፈረንስ ከተመረጡ ሰዎች ጋር ለመወያየት ሲሞክሩ ግን ከፍተኛ ውግዘትና ተቃውሞ ደርሶባቸዋል። አቶ ጣፋ በተባሉና የሕወሃት አገዛዝ ደጋፊ በሆኑ ግለሰብ
አስተባባሪነት 400 ሰዎች ብቻ በቴሌ ኮንፈረንሱ ተጋብዘው ነበር። በዚህ የቴሌ ኮንፈረንስ ላይ ራሳቸውን ለማስተዋወቅ አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን ሲናገሩ በኢትዮጵያ ለማንም የሚተርፍ ሰላምና ብልጽግና አምጥተናል ሲሉ በመኩራራት ብለዋል። በኢትዮጵያ በሁሉም አካባቢ በልማቱ ውጤት ማምጣት ሲጀምር ግን ሁሉም የተሻለ ጥቅም ለማግኘት ሲል ግጭት መፍጠር መጀመሩን ነው የገለጹት። አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን ንግግር ሲያደርጉ ሌላው ተሳታፊ ድምጽ እንዳይሰማ በመዝጋቱ ወዲያውኑ ምላሽ ያልነበረ ቢሆንም ወደ ጥያቄና መልስ ሲገባ ግን ከፍተኛ ጫጫታና ተቃውሞው ወዲያውኑ ተጀምሯል።–በቴሌ ኮንፈረንሱ ተሳታፊዎች። አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃን አንድም ጥያቄ ሳይመልሱ በተካሄደባቸው ተቃውሞ መስመሩን ለቀው ድምጻቸውን ዳግም ሳያሰሙ ከቴሌ ኮንፈረንሱ መውጣታቸውንም በሂደቱ የተሳተፉ ኢትዮጵያውያን ለኢሳት ያደረሱት መረጃ ያመለክታል።

No comments:

Post a Comment