Tuesday, January 9, 2018

የኦሮሚያ ክልል የፍትህ ቢሮ በቄሮዎች ላይ ምርመራ ማካሄድ ህገወጥ ነው አለ።

 የኦሮሚያ ክልል የፍትህ ቢሮ በቄሮዎች ላይ ምርመራ ማካሄድ ህገወጥ ነው አለ። ቢሮው ይህን ያስታወቀው የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ባለፈው ሳምንት በቄሮዎች ላይ ምርመራ እያደረኩ ነው ማለቱን ተከትሎ ነው። የቢሮው የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ ለጀርመን ድምጽ ሬዲዮ እንደተናገሩት የፌደራል ፖሊስ እያደረኩ ነው ስላለው ምርመራ የኦሮሚያ ክልል መንግስት የሚያውቀው ነገር የለም። የሃላፊው መግለጫ ምርመራው ትኩረት ለማስቀየር የታለመ ነው የሚሉ የፖለቲካ ምሁራንን አስተያየት የሚያጠናክር ነው ተብሏል። ምርመራው ስለመጀመሩ ብዙዎች ጥርጣሬ አላቸው። የህወሀት አገዛዝ ከገባበት ቀውስ ለመውጣት የህዝብን የትኩረት አቅጣጫ ያስቀይሳሉ ያላቸውን የተለያዩ የማደናገሪያ ፕሮፖጋንዳዎች ላይ መጠመዱን የፖለቲካ ምሁራን ይገልጻሉ። ባለፈው ሳምንት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሪፖርት በቀረበ ጊዜ በቄሮች ላይ ምርመራ ተጀምሯል ያሉት የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ አሰፋ አብዩ በምስራቅ ሀረርጌ በቄሮዎች እንቅስቃሴ የመንግስት መዋቅር ፈረሷል፣ እስረኞች እንዲለቀቁ ተደርገዋል፣ የመከላከያ ሰራዊት ተልዕኮ ተስተጓጉሏል ብለዋል። ለጀርመን ድምጽ ሬዲዮ ቃለመጠይቅ የሰጡት የኦሮሚያ ክልል የፍትህ ቢሮ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሃላፊ አቶ ታዬ ደንደአ የክልሉ መንግስት ስለጉዳዩ ምንም
የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ገልጸዋል። እውነትነት አለው ብዬም አላምንም ብለዋል ሃላፊው። የክልሉ መንግስት ሳያውቅ እንዲህ ዓይነት ነገር ይደረጋል የሚል እምነት እንደሌላቸው ሃላፊው ገልጸዋል። ከተደረገም ህገወጥ ነው። የኦሮሚያ ክልል መስተዳድር በፌደራል መንግስቱ የሚተላለፍን መመሪያ አልቀበልም ሲል አልያም የሃይል ርምጃ ሲወሰድ የማይቀበል መሆኑን ሲገልጽ ይህ የመጀመሪያው አይደለም። በቅርቡ በአምቦ 10የመከላከያ ሰራዊት አባላት የተገደሉበትም ሁኔታ ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው። በጨለንቆ የመከላከያ ሰራዊት ከ20 በላይ ንጹሃን ዜጎችን በገደለ ጊዜ የክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ ያለፍቃድና ጥሪ የገባውን የመከላከያ ሰራዊት ማውገዛቸው የሚታወስ ነው። በፌደራል መንግስቱ የረቀቀውን የከተማ ፕላን ዕቅድም እንዲሁ የኦሮሚያ ክልል መንግስት አልቀበልም ማለቱ ይታወሳል። ምንም እንኳን በፌደራል አወቃቀር ክልሎች የራሳቸው መብት ቢኖራቸውም በኢትዮጵያ ባለው ነባራዊ ሁኔታና በኢህአዴግ ማዕከላዊነት አሰራር እንዲህ ዓይነቱ ነገር ያልተለመደ መሆኑን የሚጠቅሱት የፖለቲካ ምሁራን በኦሮሚያ ክልል መንግስት በኩል የሚታየው እምቢተኝነት ለፌደራል ስርዓቱ ብርቱ ፈተና ሆኗል ይላሉ። የህወሀት አገዛዝ ከ25ሚሊዮን በላይ በሚሆነው የኦሮሞ ወጣት ላይ ምርመራ ጀመርኩ ማለቱ የተስፋ መቁረጥ ምልክት እንደሆነም ኢሳት ያነጋገራቸው የፖለቲካ ምሁራን ይገልጻሉ። የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ምርመራ የእውነት ከሆነ ትግሉን የበለጠ እንዲጠናከር ከማድረግ ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም ተብሏል።

No comments:

Post a Comment