Tuesday, January 9, 2018

ሁሉንም ተቃዋሚዎች ያካተተ አገራዊ ውይይት እንዲደረግ ጥሪ አቀረበ

በጂንካ የተጠራው የወላጆች ስብሰባ ሳይካሄድ ቀረ
“በመላው ኢትዮጵያ የተቀጣጠለውን ሕዝባዊ እምቢተኝነት ተከትሎ ገዥው ፓርቲ የሰጠው መግለጫ እውነተኛ የሆነ አገራዊ መግባባት እንዲፈጠር ሁሉንም የአገሪቱን ዜጋ ሊያሳትፍ ይገባል” ሲሉ የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ኅብረት /ኦህዲኅ/ ም/ሊቀመንበር አቶ ዓለማየሁ መኮንን ገለጹ።
የገዥው ህወሃት/ኢህአዴግ ባለስልጣናት ባለፈው ሳምንት በጋራ የሰጡትን መግለጫ አስመልክቶ የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ኅብረት /ኦህዲኅ/ ም/ሊቀመንበር አራት ነጥቦችን አስቀምጠዋል።
’’የጥፋቱ ወይንም የወንጀሉ ጥፋተኛ መሆናቸውንና ወንጀለኛ መሆናቸውን ማመናቸውን እንቀበላለን። ለፍትህ፣ ለሰላምና ለዴሞክራሲ የጮሁትን የጻፉትን አፍነው በማሰራቸውና ወንጀሉ የአፈናው ውጤት መሆኑን ማመናቸውን እንስማማለን። ስርዓት እንዲወገድ የኢትዮጵያ ህዝብ ጥያቄ ማንሳቱንና ብሄራዊ መግባባት መፈጠር እንዳለበት ማመናቸው መልካም ነው። ነገር ግን ብሄራዊ ጥሪ አድርገው አገር ቤት
ያሉትን፣ ነፍጥ ያነሱትን ተቃዋሚዎች ሊያካትት ይገባል። ከተቃዋሚ ፓርቲዎች በተጨማሪም የሲቪክ ተቋማት፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና ጋዜጠኞችን ያካተተ በጋራ የብሄራዊ ጥሪው አካል ሊሆኑ ይገባል። ይህ ሳይሆን ግን በተለመደው በቀደመው የሃሰት መንገድ ለመጓዝ ከፈለጉ ግን ምርጫው የእነሱ ነው። ይህን ተከትለው ካላደረጉ ግን ሕዝቡ ጠራርጎ ይወስዳቸዋል።’’ ሲሉ እውነተኛ የሆነ ብሄራዊ የለውጥ ተሃድሶ ጥሪ እንዲደረግ ሲሉ አቶ ዓለማየሁ መኮንን በፓርቲያቸውና በራሳቸው ስም ጥሪ አቅርበዋል።
በሌላ በኩል ባለፈው ሳምንት ገዥው ፓርቲ በደቡብ ክልል መምህራንን፣ ወላጆችንና ተማሪዎች ለማወያየት የጠራው ስብሰባ ሳይሳካ ቀርቷል። ለሶስት ቀናት በተደረገው የመምህራን ውይይት ላይ የስድስት ወራት የደመወዝ ጭማሪ ደመወዛቸው እንደሚከፈላቸው ስምምነት ላይ ተደርሶ ነበር። ነገርግን የታህሳስ ወር የአንድ ወር ደመወዝ ብቻ ተከፍሎዋቸው የአምስት ወራት የደመወዛቸው ጭማሪ ባለመከፈሉ አሁንም በመምህራን ዘንድ ቅሬታን ፈጥሯል። በክልሉ ያሉት የመምህራን ማህበራት የመምህራኑን ቅሬታዎች ለሚመለከተው አካል በማቅረብ የመፍትሄ አካል ከመሆን ይልቅ የገዥው ፓርቲ አገልጋይ ሆነዋል። መምህራኑ ለትምህርት ጥራትና ለመብታቸው ትግላቸው አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በአንድ ድምጽ ስምምነት ላይ ደርሰዋል።
ለአንድ ቀን በተጠራው የወላጆች ስብሰባ ወላጆች ስርዓቱ በተለመደው የማዘናጊያ ጊዜ መግዣ ውይይት ላይ አልተገኙም። የወላጆችን ውሳኔ ተከትሎ በጂንካና አካባቢው ያሉት የአገዛዙ ካድሬዎች ያሰቡት ሳይሳካ ውይይቱ ተቋርጧል። ተማሪዎች በበኩላቸው አወያዮቹን በጥያቄ አፋጠዋል። ‘’በዚህ የፈተና ወቅት ለመምህራን፣ ለወላጆችና ለተማሪዎች ውይይት ብላችሁ አንድ ሳምንት ሙሉ አባከናችሁብን?’’ በማለት በአንደኛ ሴሚስተር ፈተና ወቅት ጊዜ መገደሉን በጋራ አውግዘዋል።

No comments:

Post a Comment