Thursday, January 4, 2018

በኢትዮጵያ ወህኒ ቤት የሚገኙ ፖለቲከኞችና ሌሎች እስረኞች ለሀገራዊ መግባባት ሲባል እንዲፈቱ ተወስኗል በሚል በመንግስት የተሰጠው መግለጫ በመንግስት ሲሰረዝና ሲደለዝ መዋሉ ታወቀ

 በኢትዮጵያ ወህኒ ቤት የሚገኙ ፖለቲከኞችና ሌሎች እስረኞች ለሀገራዊ መግባባት ሲባል እንዲፈቱ ተወስኗል በሚል በመንግስት የተሰጠው መግለጫ በመንግስት ሲሰረዝና ሲደለዝ መዋሉ ታወቀ። የጠቅላይ ሚኒስትሩ መግለጫ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት ማህበራዊ ገጽ ላይ ሰባት ጊዜ እየተሰረዘና እየታረመ መጻፉ ታውቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለም የመንግስት መግለጫን ተከትሎ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶችና ሌሎች ወገኖች በጉዳዩ ላይ አስተያየት ሰጥተዋል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል የሰቆቃው ዘመን ፍጻሜ እንደሚሆን ተስፋውን ሲገልጽ ሂውማን ራይትስ ዎች ውሳኔው መቼና እንዴት ተግባራዊ ይሆናል ሲል ጠይቋል። አቃቢ ሕግ ጉዳያቸው በሕግ ተይዞ በእስር ላይ የሚገኙ የተለያዩ ፖለቲከኞች የተሻለ ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠርና የዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት በማሰብ ክሳቸው ተቋርጦ እንዲለቀቁ ተወስኗል በሚል በቅድሚያ ይፋ የሆነው መግለጫ በሶስት ሰአታት ጊዜ ውስጥ ስድስት ጊዜ ተሰርዞና ተደልዞ ለሰባተኛ ጊዜ የቀረበው መግለጫ በወንጀል የተፈረደባቸውና በወንጀል የተጠረጠሩ የሚለውን ጨምሮ ቁጥሩንም አንዳንድ በሚል ገድቦታል። ሕገመንግስቱ በሚፈቅደው የሚል በመጨመርና ማጣራት በማድረግ የሚለውን በማከል በሕገመንግስቱ መሰረት የሚለውን በመጨመር በሶስት ሰአታት ውስጥ ሲሰረዝና
ሲታረም ቆይቷል። በቅድሚያ በይቅርታ ይወጣሉ የተባለው በምህረት በሚል እንዲስተካከል ተደርጓል። ምህረት ታሳሪዎቹ ጥያቄ ማቅረብ ሳይኖርባቸው በአሳሪው አካል ውሳኔ የሚፈጸም መሆኑንም መረዳት ተችሏል። ይህ በእንዲህ እንዳለም አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል የመንግስትን ርምጃ በበጎ የተመለከተው ሲሆን የአሰቃቂው የጭቆና ዘመን ማብቂያ ሊሆን ይችላል ሲልም ተስፋውን ገልጿል። በፖለቲካዊ ምክንያቶች በተቃኙና በሀገራት የተቀነባበሩ ክሶች በወህኒ ለሚገኙ እስረኞች ግን ውሳኔው የዘገየ ነው ሲልም አስተያየቱን ሰጥቷል። ውሳኔው ሙሉ በሙሉ በፍጥነት ተግባራዊ እንዲሆን የጠየቀው መግለጫውን በብሪታኒያ ለንደን ያደረገው አምነስቲ ኢንተርናሽናል የጸረ ሽብር ህጉን ጨምሮ ለእስሩ ምክንያት የሆኑ ጨቋኝ ሕጎችም እንዲሰረዙ ጠይቋል። በኢትዮጵያ ውስጥ የሚፈጸሙ የሰብአዊ መብት ረገጣዎችን በቅርበት በመከታተል የሚታወቀው መቀመጫውን በአሜሪካ ኒዮርክ ያደረገው ሒዩማን ራይትስ ዎች ውሳኔው መቼና እንዴት ተግባራዊ ይሆናል የሚለው ባይታወቅም በሀገሪቱ የሰፈነውን ጭቆና ለማብቃት ወሳኝ ርምጃ ነው ሲል ገልጿል። የማዕከላዊ ምርመራ እስር ቤትን ዘግቶ እስረኞችን ወደ ሌላ ቦታ አግዞ ተመሳሳይ ስቃይ ከፈጸመ ውሳኔው ትርጉም የለሽ ይሆናል ሲልም አሳስቧል። ቢቢሲ ለንደን ላይ ያነጋገራቸው የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ባለቤት ወይዘሮ የምስራች ሃይለማርያም በመንግስት መግለጫ መሰረት አቶ አንዳርጋቸው እንደሚፈቱ ተስፋ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ሆኖም እነማንና መቼ ይፈታሉ የሚለው ግን በግልጽ ስላልተቀመጠ ጥርጣሬያቸውን አክለዋል።

No comments:

Post a Comment