Monday, January 29, 2018

በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ በተከሰተው ግጭት የተፈናቀሉት ሰዎች ቁጥር 1 ሚሊየን ያህል መድረሱን አለም አቀፍ ሪፖርቶች አመለከቱ።

ፋይል ስደተኞቹ በ4 መቶ ጣቢያዎች መስፈራቸውን ሪፖርቱን ያቀረቡት ተቋማት ገልጸዋል። ተፈናቃዮቹ በቂ እርዳታ እየተደረገላቸው አለመሆኑንም በሪፖርቱ ተመልክቷል። በኦሮሚያና ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች የተፈናቀሉት ኢትዮጵያውያን በተለያዩ የሃገሪቱ አካባቢዎች በተበራከተው ግጭት ምክንያት ተዘንግተዋል። በቀደሙ ሪፖርቶች 7 መቶ ሺ ሕዝብ መፈናቀሉ ሲነገር ነው የቆየው። ኦቻ የተባለው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተቋም ከብሔራዊ አደጋና መከላከል ኮሚሽን ጋር ባካሄደው ጥናት ግን በሶማሌና ኦሮሚያ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የተፈናቀሉት ሰዎች ቁጥር 1 ሚሊየን ያህል ተጠግቷል። እንደ ሪፖርቱ ገለጻ 857 ሺ የሚሆኑ ዜጎች መፈናቀላቸው ሲረጋገጥ ቁጥሩ ከዚህም ሊልቅ የሚችልበት ሁኔታ አለ። በሁለቱም አጎራባች ክልሎች ያለው ግጭት አሁንም እንዳልበረደ ሪፖርቱ አመልክቷል። ተፈናቃዮቹ በ4 መቶ መጠለያ ጣቢያዎች ሰፍረው እንደሚገኙም ነው ሪፖርቱ የገለጸው። ከሶማሊያ የተፈናቀሉት የኦሮሞ
ተወላጆች ከፍተኛውን ቁጥር ይዘዋል። በሪፖርቱ እንደተመለከተው ከተፈናቀሉት 1 ሚሊየን ሰዎች 68 ሺ የሚሆኑት ሶማሌዎች ናቸው። ቀሪዎቹ ግን ኦሮሞዎች መሆናቸው ነው የተነገረው። ተፈናቃዮቹ በቂ እርዳታ እየተደረገላቸው አለመሆኑም በሪፖርቱ ተገልጿል። በመጠለያ ጣቢያዎች ከሰፈሩት በተጨማሪ በየዘመድ ቤቱና ተረጂዎችን ለማስጠጋት ፈቃደኛ በሆኑ ሰዎችም የሚረዱ አሉ ተብሏል። ከተፈናቃዮቹ መካከል አስቸኳይ እርዳታ የሚፈልጉት 110 ሺ አባወራ ቤተሰቦች እንደሆኑ ነው የተነገረው። ከነዚሁም ውስጥ 58 ሺ አባወራዎች ከኦሮሚያ ሲሆኑ 41 ሺ ያህሉ ደግሞ ከሶማሌ ክልል ናቸው ሲል ገልጿል ሪፖርቱ። በግጭቱ ሳቢያ ከተፈናቀሉት መካከል 93ሺ የሚሆኑ ሕጻናት ትምህርታቸውን ማቋረጣቸው ተነግሯል። እናም እነዚህ ልጆች በአስቸኳይ ጊዜ የትምህርት አቅርቦት ዘዴ ያቋረጡትን ትምህርት እንዲጀምሩ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ነው የተገለጸው። 52ሺ አርብቶ አደሮች ደግሞ ከብቶቻቸውን በግጦሽ ማጣትና በውሃ እጥረት ከፍተኛ ችግር ላይ ናቸው ተብሏል። በኦሮሚያና ሶማሌ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የተፈናቀሉት 1 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች በውሃ እጦት ከፍተኛ ስቃይ ላይ መሆናቸው ታውቋል።

No comments:

Post a Comment