Tuesday, January 23, 2018

በምስራቅ ሸዋ ዞን በአለም ጤና ከተማ በመካሄድ ላይ ባለው ህዝባዊ ተቃውሞ ቢያንስ 3 ሰዎች ተገደሉ

ዛሬ ጥር 15 ቀን 2010 ዓም በተለያዩ የኦሮምያ ክልል ከተሞች የተቃውሞ ሰልፎች የተካሄዱ ሲሆን፣ የአጋዚ ወታደሮችም ለተቃውሞ በወጡት ዜጎች ላይ በቀጥታ በመተኮስ የሰው ህወይት አጥፍተዋል። በምስራቅ ሸዋ ዞን በአለም ጤና ከተማ ቢያንስ 3 ሰዎች በጥይት የተመቱ ሲሆን፣ በርካታ ሰዎችም ቆስለዋል። ከተመቱት መካከል አንዱ ህይወቱ ወዲያውኑ ሲያልፍ የሌሎች እጣ ፋንታ አልታወቀም። በአጋዚ ድርጊት የተበሳጩ የከተማዋ ነዋሪዎች በተሽከርካሪዎች ላይ ድንጋይ በመወርወር ጉዳት አድርሰዋል። አካባቢው ለተሽከርካሪ ዝግ ሆኗል። በወለጋ መንዲ ከተማም እንዲሁ የተቃውሞ ሰልፍ ሲደረግ ውሎአል። 

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በአለም ጤና አካባቢ ባለው ችግር ምክንያት ሰራተኞቹ ወደ ሞጆ እና አዋሳ ከመንቀሳቀሳቸው በፊት መረጃዎችን ከድርጅቱ የጸጥታ ማእከላት እንዲጠይቁ መክሯል።
በኦሮምያ የታየው ህዝባዊ አመጽ ተረጋግቷል በሚል የገዢው ፓርቲ ባለስልጣናት መግለጫ ሲሰጡ ነበር።
በሌላ በኩል በምስራቅ ሸዋ ዞን በቦሰት ወረዳ በቦፍ ከተማ በሆቴል እና በሸቀጥ ማከፍፈል ስራ የሚተዳደር ክብረት አበበ የተባለ የህወሃት አባል አምና የወጣውን የአስቸካይ ግዜ አዋጅ ሽፋን በማድረግ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን እየመራ የአካባቢውን ህዝብ ሲያሳስር እና ሲያስገድል መቆየቱን በመቃወም ከከተማው እንዲወጣ ያካባቢው ህዝብ በተደጋጋሚ ሲያስጠነቅቅና ድርጅቱና መኖሪያ ቤቱ ላይ ወረቀት በመለጠፍ ሲያስጠነቅቅ ቢቆይም፣ ግለሰቡ ፈቃደኛ ባለመሆኑ፣ ትናንት 5 ሰአት አካባቢ ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች በ4 ጥይቶች ተደብድቦ መገደሉን ከስፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
ከኦሮምያ ክልል ዜና ሳንወጣ ኦህዴድ በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ለ17 ቀን የተወያየበትን አጀንዳ ለመካከለኛ እና ዝቅተኛ አመራሩ ለማወያየት ለዞን፣ለወረዳ፣እንዲሁም እስከ ቀበሌ ድረስ ላሉት የምክር ቤት የድርጅት አባላት ስብሰባ መጥራቱን ለድርጅቱ አባላት ከተላከው የጥሪ ወረቀት ለመረዳት ተችሎአል።

No comments:

Post a Comment