Tuesday, January 9, 2018

የሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ/ሕወሃት/ንብረት የሆነው ኤፈርት በ745 ሚሊየን ብር ያስገነባው የወርቅ ማምረቻ ፋብሪካ ስራ ጀመረ።

የመንግስት መገናኛ ብዙሃን እንደዘገቡት በሳምንት 1 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር የሚያስገኘው ይህ ፋብሪካ በቀን እስከ 5 ኪሎ ግራም ወርቅ ያመርታል። ኤፈርት ከዚህም በተጨማሪ በመላዋ ትግራይ የማዕድን ማልማት ስራዎችን ለማከናወን ከ8 የአሜሪካና የካናዳ ኩባንያዎች ጋር ስምምነት ላይ ደርሷል። በዚህ ስምምነት መሰረትም በትንሹ በአመት ከአንድ ቢሊየን ዶላር በላይ ገቢ ለማስገኘት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን የኤፈርት ዋና ሃላፊ ወይዘሮ አዜብ መስፍን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን እንደዘገበው ትላንት በሽሬ እንደስላሴ የተገነባው ይህ የወርቅ ፋብሪካ ኢሕአዴግ ወደ ስልጣን ከመጣ ወዲህ የተገነባ የመጀመሪያው ፋብሪካ ነው። በኢትዮጵያ ከ33 አመታት ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገነባ እንደሆነም ተመልክቷል። ሌላው የሕወሃት ንብረት የሆነው መስፍን ኢንጂነሪንግ እንደገነባው የተገለጸው ይህ የወርቅ ፋብሪካ 745 ሚሊየን ብር እንደወጣበትም ታውቋል። ሜሌ የሚል ስያሜ የተሰጠው ይህ የወርቅ ፋብሪካ በቀን ከ4 እስከ 5
ኪሎግራም ወርቅ እንደሚያመርትም የፋብሪካው ሃላፊዎች ገልጸዋል። ፋብሪካው በመጀመሪያ የሙከራ ምርቱ በ5 ቀናት ከ18 ኪሎግራም በላይ ወርቅ ያመረተ ሲሆን በጥራቱም ከፍተኛ እንደሆነ ተገልጿል። ጥራቱ 23 ካራት የሆነ ወርቅ ያምርታል የተባለው ይህ ፋብሪካ በሳምንት 1 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር እንደሚያስገኝም ሃላፊዎቹ ተናግረዋል። አመታዊ ገቢውም ከ40 ሚሊየን ዶላር በላይ እንደሆነም አስታውቋል። የኤፈርት ዋና ሃላፊ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወይዘሮ አዜብ መስፍን እንደተናገሩት ከዚህ በተጨማሪ ሌላ የቢሊየን ዶላሮች ፕሮጀክቶች በሂደት ላይ ይገኛሉ። ከ8 የአሜሪካና የካናዳ ኩባንያዎች ጋር ኤፈርት በጋራ ለመስራት ባቀዳቸው የወርቅና መሰል ፕሮጀክቶች በአመት በትንሹ አንድ ቢሊየን ዶላር እንደሚያገኝም አስታውቀዋል። በወይዘሮ አዜብ መስፍን የሚመራው የሕወሃት ንብረት የሆነው ኤፈርት ስራውን ሲጀምር ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የወሰደውን የ1 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር ብድር የተበላሸ በሚል ከነወለዱ የተሰረዘለት መሆኑ ይታወሳል። አሁንም ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ በኩባንያዎቹ ስም ብድር በመውሰድ ላይ መሆኑም ታውቋል።

No comments:

Post a Comment