Tuesday, October 31, 2017

የህወሃት አመራሮች በኦሮምያ ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማወጅ ያደረጉት እቅድ አልተሳካም

ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ አንድ የኦህዴድ የአመራር አባል እንደገለጹት በአቶ አባይ ጸሃዬ የተመራ 5 ነባር የህወሃት አመራሮችንና ሌሎችን ታማኝ ሰዎችን የያዘ ቡድን፣ በኦሮምያ ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማወጅ ውሳኔ አሳልፎ የነበረ ቢሆንም፣ መረጃው አፈትልኮ በመውጣቱ ሳይሳካ ቀርቷል። ቡድኑ እስከ ጥቅምት 29 ቀን 2010 ዓም በተለያዩ ከተሞች ፈንጅዎች እንዲፈነዱና ጥቅምት 30 ቀን 2010 ዓም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ተጠርቶ በኦሮምያ ክልል “ ህዝብ እየተገደለ በመሆኑ፣ አስቸኳይ አዋጅ መታወጅ አለበት” የሚል ውሳኔ ለማሳለፍ አቅዶ እንደነበር ባለስልጣኑ ተናግረዋል።

በስብሰባው ላይ ከተሳተፉት የህወሃት አመራሮች መካከል አንደኛው መረጃውን ለአቶ ለማ መገርሳ መስጠቱንና አቶ ለማም በክልሉ ምንም አይነት የተቃውሞ ሰልፍ እንዳይደረግ ትእዛዝ ማስተላለፋቸውን ምንጫችን ገልጸዋል። ይሁን እንጅ ህዝቡ የኦህዴድን ትእዛዝ ባለመቀበል ተቃውሞውን በራሱ መንገድ በመቀጠሉ የሚያደርገው አማራጭ ያጣው የአቶ ለማ አስተዳደር፣ የኦሮምያ ልዩ ሃይልን በማሰማራት ተልዕኮ የተሰጣቸውን ሰዎች ወደ ማደን መግባቱንና የተያዙትን ሰዎች ብሄራቸውን እየጠቀሰ በክልሉ ቴሌቪዝን እንዲቀርቡና በተዘዋዋሪ ለህወሃት መሪዎች “ ደርሰንባችሁዋል” የሚል መልዕክት ለማስተላልፍ መሞከሩን ምንጮች ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለያዩ አካባቢዎች የተያዙ ሰዎች ውሳኔውን ለማስፈጸም የተላኩ እንደነበር የሚገልጹት ምንጮች፣ መረጃው በኢህአዴግ ድርጅቶች መካከል ያለውን አለመግባባትና አለመተማመን ጨምሮታል። መረጃው ሆን ተብሎ በክልሉ የሚያካሄደውን የአደባባይ ላይ ተቃውሞ ለማስቆም በማሰብ ለአቶ ለማ እንዲነገራቸው ታቅዶ ይሁን ወይም የህወሃት የደህንነት አባላት በትክክል በክልሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለማወጅ ፍላጎት ኖሮአቸው ያወጡት እቅድ ይኑር አይኑር እንደማይታወቅ የገለጹት ምንጫችን፣ መረጃው አቶ ለማ በሚቀርቡት ሰው በኩል እንደደረሳቸውና እሳቸውም ትእዛዙን እንዳስተላለፉ ገልጸዋል። አቶ ለማ ተሰሚነት አሏቸው ለሚሉዋቸው ሃይሎች ሁሉ ሰልፉ እንዲቆም መረጃ እንዲደርሳቸው ትእዛዝ መስጠታቸውን የሚገልጹት ምንጮች፣ ይሁን እንጅ ህዝቡ ተቃውሞውን እንደማያቆም የተረዳው የአቶ ለማ አስተዳደር ግራ ተጋብቶ መሰንበቱን ተናግረዋል።
የትግራይ ክልል የህዝብ ግንኙነት ቢሮ በኦሮምያ ክልል ተያዙ የተባሉ ሰዎች ብሄራቸው እየተጠየቀ በክልሉ የቴሌቪዥን ጣቢያ መነገሩ እንዳበሳጨውና ጣቢያው ከዚህ ድርጊቱ የማይቆጠብ ከሆነ የራሱን አማራጭ እንደሚወስድ የሚገልጽ መግለጫ መዋውጣቱ ይታወሳል።
የኢህዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ በኢህአዴግ እህት ድርጅቶች መካከል ያለው አለመተማመን መጨመሩን አምኖ በኢህአዴግ እህት ድርጅቶች የጋራ አላማ ዙሪያ በትግል ላይ የተመሰረተ ጓዳዊ ትስስር ይበልጥ እንዲዳብር ለማድረግ በተለዬ ሁኔታ እሰራለሁ ብሎአል።
በሌላ በኩል ግን በነቀምቴ ከተማ በነበረው ህዝባዊ የለውጥ እንቅስቃሴ የተገደሉት ሰዎች የትግራይ ተወላጆች እንደሆኑ ተደርጎ በማህበራዊ ሚዲያ የተዘገበው ትክክል አለመሆኑን የኦሮምያ ክልል የኮሚኒኬሽን ሃላፊ አቶ አዲሱ አረጋ ገልጸዋል። የነቀምቴ ከተማ ፖሊስ ፅህፈት ቤት ሃላፊ ኮማንደር ጌታቸው ይታና አምስቱ የኦሮሞ፣ ሶስት ጉራጌዎች እና ሁለት የትግራይ ብሄሮች ተወላጆች ጉዳት ሲደርስባቸው፣ አንድ የኦሮሞ እና ሁለት የአማራ ብሄር ተወላጆች ደግሞ መገደላቸውን የህወሃት ንብረት ለሆነው ፋና ሬዲዮ ተናግረዋል።
የህወሃት ደጋፊዎች በኦህዴድ አመራሮች ላይ ጠንካራ የማህበራዊ ሚዲያ ዘመቻ ከፍተዋል። በክልሉ ህይወታቸው ለሚያልፈው የትግራይ ተወላጆች የኦህዴድ መሪዎች ተጠያቂዎች ናቸው በማለት ዛቻ የተሞላበት ጽሁፎችን እየጻፉ ነው። የህወሃት የፕሮፓጋንዳ ክፍል አባል ተደርጋ የምትቆጠረው እና ዛሚ ኤፍ የሚል ሬዲዮ ያላት ወ/ሮ ሚሚ ስብሃቱ የኦህዴድ መሪዎች በአገሪቱ እየደረሰ ለላው ጥፋት ተጠያቂ ናቸው በማለት በይፋ ክስ ስታሰማ ቆይታለች።

No comments:

Post a Comment