Tuesday, June 28, 2016

የህወሃት አባላት ያልሆኑ የደህንነት አባላት በጥርጣሬ እየታሰሩ ነው

ሰኔ ፳፩ ( ሃያ አንድ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት አባል የነበሩና በደህንነት መስሪያ ቤት ውስጥ በተለይም በሶማሊያ በሚካሄደው ወታደራዊ ዘመቻ ላይ ቁልፍ ሚና ነበራቸው የተባሉ 3ቱ ነባር የደህንነት አባላትና አስተባባሪዎች ከተገደሉ በሁዋላ፣ ከግድያው ጀርባ እጃቸው ሊኖርበት ይችላል ተብለው የተጠረጠሩ የህወሃት አባላት ያልሆኑ የሌሎች ብሄረሰቦች የደህንነት አባላት እየተያዙ ነው። እስካሁን ከተያዙት መካከል አብዛኞቹ የኦሮሞ ተወላጅ የደህንነት አባላት ሲሆኑ፣ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጠበቂዎችም ይገኙበታል።

በአልሸባብ ተይዘው የነበሩትን የኢትዮጵያን ወታደሮች እና አንድ የፈረንሳይ የስለላ አባል ለማስለቀቅ ተልእኮ ተሰጥቷቸው የነበሩና ተልእኮዋቸውን በስኬት የተወጡ ኮማንዶችም ታስረዋል።  ኮማንዶዎቹ ታጋቾችን ሲያስለቅቁ ከአሜሪካና ከአውሮፓ ህብረት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚከፈላቸው ቃል ተግብቶላቸው የነበረ ሲሆን፣ ተልእኮዋቸውን ከፈጸሙ በሁዋላ ግን አብዛኛውን ገንዘብ ወታደራዊ አዛዦች እንደነጠቁዋቸው፣ ይህንንም በመቃወማቸው ለእስር ተዳርገው እንደበሩ ታውቋል። ከአሁኑ ግድያ ጀርባ እጃቸው ሊኖርበት ይችላል በሚል የተወሰኑት ተይዘው በድጋሜ ታስረዋል።

ምንም እንኳ ግድያዎችን በመመርመር ላይ ያለው ኮሚቴ፣ 9ኙን የደህንነት አባላት ማን ገደላቸው በሚለው ዙሪያ ድምዳሜ ላይ ባይደርስም ፣ ከግድያው ጀርባ የውጭ እጅ አለበት ከሚለው መላ ምት ይልቅ በመስሪያ ቤቱ ውስጥ ከሚታዬው የብሄር ልዩነትና ጸብ ጋር የተያያዘ ነው የሚለውን መላ ምት ወደ መቀበል እያዘነበሉ ነው ። በደህንነቱ ውስጥ የተፈጠረው ክፍተት በተለይ ለአልሸባብ እየጠቀመው መምጣቱን የሚገልጹት ምንጮች፣  ሶስቱ ወሳኝ ሰዎች መገደላቸውን ተከትሎ በሶማሊያ ያለው የመከላከያ ሰራዊት ጨለማ ውስጥ መውደቁን ይናገራሉ።
የደህንነት አባላት እንደሚሉት ሰሞኑን ደግሞ ጥርጣሬው እየሰፋ ሄዶ ከህወሃት አባላት ውጭ ያሉ የሌሎች ብሄረሰቦች የደህንነት አባላት አንድ በአንድ እየተጠሩ በመመርመር ላይ ናቸው።
ምንጮቻችን ከህወሃት ውጭ ያሉ የደህንነት አባላት በሞላ  ከአጋዚ ገዳይ ስኳድ ራሳቸውን ለመከላከል ጥንቃቄ እንዲያደርጉ፣ በተለይም መሳሪያቸውን እንዲያስረክቡ ሲጠየቁ ፈቃደኛ እንዳይሆኑ ለጓደኞቻቸው ምክር ያስተላልፋሉ። መርማሪዎች በሚጠሩዋቸው ጊዜም መሄድ እንደሌላበቸው ይመክራሉ።
ቁልፍ የደህንነት አባላት መገደላቸውን ተከትሎ በደህንነት መስሪያ ቤቱ ውስጥ ከፍተኛ ፍርሃት መንገሱን ኢሳት መዘገቡ ይታወሳል። ግድያውን የሚፈጽሙት የተለያዩ የውጭ ሃይሎች ሊሆኑ ይችላል የሚሉ መላምቶች ቀርበው ምርመራ ሲደረግ ቆይቷል። አሁን የሚታዬው የሌሎችን ብሄረሰብ አባላትን ከድህነት መስሪያ ቤቱ ሙሉ በሙሉ የማስወጣቱ እርምጃ ከቀጠለ ፣ የእርስ በርስ መጠፋፋቱ ሊቀጥል እንደሚችል ምንጮች ግምታቸውን ያስቀምጣሉ።

No comments:

Post a Comment