Thursday, June 9, 2016

ኢትዮጵያ ያጸደቀችው የኢንተርኔት አጠቃቀም ህግ ተቃውሞ ገጠመው

የኢትዮጵያ መንግስት የኢንተርኔት አጠቃቀም ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን ለመከላከል በሚል ማክሰኞ የጸደቀውን አዋጅ ተከትሎ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቋማት በህጉ ላይ ቅሬታ ማቅረብ መጀመራቸውን አለም አቀፉ መገናኛ ብዙሃን ረቡዕ ዘገቡ።
እስከ 10 አመት የሚደርስ ቅጣትን ያስተላልፋል የተባለው ይኸው አዲስ ህግ፣ በሃገሪቱ ሃሳብን ለመግለጽ በሚደረገው ጥረት ላይ ተጨማሪ ቁጥጥርን እንደሚያጠናክር የሰብዓዊ መብት ተሟጋች አካላት በመግለጽ ላይ መሆናቸው ፎክስ ኒውስ አስነብቧል።

አዲሱ አዋጅ የሃገሪቱ ዜጎች ሃሳባቸውን በተለያዩ ድረ-ገጾች ላይ ለመግለፅና ለመወያየት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ላይ ጥብቅ ክትትልንና ቁጥጥርን የሚያደርግ ሲሆን፣ ስም የሚያጠፉ ጽሁፍንና መልዕክትን አስተላልፈዋል የተባሉ ግለሰቦች በትንሹ በሶስት አመት እስራት እንደሚቀጡ በህጉ ተደንግጓል።
ይሁንና፣ የኢትዮጵያ መንግስት ህጉን ያፀደቀው ዜጎች ሃሳባቸውን በነጻነት በመግለጽ በሚያደርጉት ትግል ላይ ቁጥጥርን ለመዘርጋት ያለመ መሆኑን ሂውማን ራይትስ ዎችና በርካታ ድርጅቶች ይገልጻሉ።
መንግስት የረቀቁ የኢንተርኔትና የስለላ መፈጸሚያ አገልግሎቶችን በውድ ዋጋ በመግዛት በመጠቀም ላይ መሆኑ በተለያዩ አካላት ይፋ ቢደረገም ባለስልጣናት በየዕለቱ ከ1ሺ የሚበልጡ የኢንተርኔት የስለላ ጥቃቶች በመንግስታዊ ተቋማት ይፋጸማሉ ሲሉ አስታውቀዋል።
ይሁንና ጥቃቱ በማን አካልና እንደተፈጸመና ስለደረሰው ጉዳት የተሰጠ ዝርዝር መርጃ የለም።
በአዲሱ አዋጅ ላይ ቅሬታን እያቀረቡ ያሉት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ግለሰቦች ድርጊቱ በሃገሪቱ ያለውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሊያባብሰው እንደሚችል ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ መሆናቸው ይታወቃል።
ኒውስ 24 የተሰኘ የደቡብ አፍሪካ ታዋቂ ጋዜጣ በበኩሉ የአዋጁ መፅደቅን ተከትሎ ከበርካታ አካላት ተቃውሞና ትችቶች እየቀረቡ እንደሚገኝ ረቡዕ ለንባብ ባበቃው እትሙ አስፍሯል።
የዚህኑ ረቂቅ አዋጅ መዘጋጀት ተከትሎ ኢትዮ-ቴሌኮም በሃገሪቱ ውስጥ ያሉ ተንቀሳቃሽ ስልኮች ለመመዝገብ መመሪያ አውጥቶ ለሚመለከተው አካል ማስተላለፉ ይታወሳል።
በኩባንያው ያልተመዘገቡ የእጅ ስልኮች አገልግሎት እንዳይሰጡ የሚደረግ አሰራርን ተግባራዊ ለማድረግ አስፈላጊው ቁሳቁስ መሟላቱን የኢትዮ-ቴሌኮም ባለስልጣናት ይፋ ማድረጋቸውን መዘገባችን ይታወቃል።

No comments:

Post a Comment