Thursday, April 7, 2016

በአበረታች መድሃኒት ምክንያት የኢትዮጵያ አትሌቶችና አትሌቲክስ ማኅበር ቅጣት ይጠብቃቸዋል

መጋቢት ፳፱( ሃያ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ ውስጥ ተደርጎ የማያውቅ ድርጊቶች በቅርቡ ከዓለምአቀፉ አትሌቲክስ ማኅበርና ከመገናኛ ብዙሃን በኩል መደመጥ ተጀምርዋል። ውጤታማው የኢትዮጵያ የመሃከለኛና የረዥም ሩጫ ተወዳዳሪዎች አበረታች መድሃኒት መጠቀማቸውን የፀረ አደንዛዥ እጽ ተቆጣጣሪ ድርጅት በምህጻረ ቃሉ ዋዳ /WADA/ አስታውቋል።

ዓለምአቀፉ አትሌቲክ ማኅበር የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ማኅበር የሯጮችን የደም ምርመራ ናሙና ውጤት ካላቀረበ በኢትዮጵያ ላይ ቅጣት እንደሚጥል ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ማኅበር የሕክምና ኃላፊ የሆኑት ዶክተር አያሌው ጥላሁን እንዳሉት ”ከ150 አስከ 200 በሚሆኑ ሯጮች ላይ በቅርብ ሳምንታት ውስጥ ምርመራ እንደሚጀምር ገልጸዋል።
ዶክተር አያሌው አክለውም ”እኛ ምርመራውን ካላደረግን በቅርቡ ከማንኛውም ውድድሮች የሚያግድ ቅጣት እንደሚጣልብን ዓለምአቀፉ አትሌቲክስ ማኅበር አሳውቆናል” በማለት የሁኔታውን አሳሳቢነት ተናግረዋል።
የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ማኅበር ፕሬዝዳንት ሰር ሰባስቲያን ኮባሳለፍነው ወር ላይ እንዳሉት ኢትዮጵያ ከዋነኞቹ ተጠርጣሪዎቹ አምስቱ አገራት ሩሲያ፣ ኬንያ ፣ ሞሮኮ፣ ቤላሩስና ዩክሬን ተርታ መመደቧን አሳውቀዋል።
ኢትዮጵያና ኬንያ እያንዳንዳቸው ሶስት ሯጮች ላይ እገዳ መጣላቸውን አስታውቀዋል። ዘጠኝ የኢትዮጵያ ሯጮች አበረታች መድሃኒት ሳይጠቀሙ እንዳልቀሩ ጥርጣሬ መኖሩንና ማጣራቱንም እንደሚቀጥል ማኅበሩ አስታውቋል።
የአበረታች መድሃኒት ቁጥጥሯ ደካማ የተባለችው ሩሲያ ከማንኛውም ውድድሮች የታገደች ሲሆን ኬኒያና ኢትዮጵያም አስቀድመው ካላሳወቁ እገዳውን ሊጥል እንደሚችል ዓለምአቀፉ አትሌቲክ ማኅበር ማስጠንቀቂያ መስጠቱን አሾሸትድ ፕሬስ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment