Wednesday, April 13, 2016

በኢትዮጵያ 84ሺህ ብቻ የተመዘገቡ ተሽከርካሪዎች መኖራቸውን CNN ዘገበ

ዜና (ሚያዚያ 5 ፥ 2008)

በአፍሪካ ባሉት 97 ሚሊዮን ህዝብ ቁጥር በአህጉሪቱ ከናይጀሪያ ቀጥላ በሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ፣ 84ሺህ የተመዘገቡ ተሽከርካሪዎች ብቻ እንዳሏት ተገለጠ።
በጉዳዩ ዙሪያ ልዩ ዘገባን ያቀረበው ሲኤንኤን (CNN) የቴለቪዥን ጣቢያ ሃገሪቱ ከውጭ በሚገቡ ተሽከርካሪዎች ላይ 35 በመቶ ታክስን እንደምታስከፍልም አመልክቷል።
አብዛኞቹ ተሽከርካዎች ከውጭ ሃገር የገቡ መሆናቸውን ያወሳው የቴለቪዥን ጣቢያው በአሁኑ ወቅት 84ሺህ ተሽከርካሪዎች መኖራቸውን ባቀረበው ሪፖርት አስፍሯል።

በሃገሪቱ ያሉ ያረጁ ተሽከርካሪዎችም በአካባቢ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ እየፈጠሩ እንደሚገኝና ለመለዋወጫ ግዢም ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እንደሚወጣ በአዲስስ አበባ ዩኒቨርስቲ የማህበረሰብ ፖሊሲ የሆኑት ኮንስታንቲኖስ ብሩህተስፋ ለቴሌቪዥን ጣቢያ አስረድተዋል።
በኢትዮጵያ ያለው አነስተኛ የተሽከርካሪ ቁጥር ግምት ውስጥ በማስገባትም የቻይና ኩባንያዎች በሃገሪቱ ተሽከርካሪን መገጣጠም እንደጀመሩም ሲኤንኤን (CNN) ኩባንያዎቹን ዋቢ በማድረግ አቅርቧል።
ሃገሪቱ እስከባለፈው አመት ድረስ ያላት የተመዘገቡ 84ሺህ ተሽከርካሪዎችም ከ97 ሚሊዮን ህዝብ ቁጥር ጋር ሲነጻጸር እጅግ አነስተኛ መሆኑን የቴለቪዥን ጣቢያው በሪፖርቱ አመልክቷል።
15 አመት የሞላቸውና ከዛ በላይ የሆኑ ተሽከርካሪዎችም እስከ 16 ሺህ ዶላር ድረስ እንደሚሸጡ በመኪና ንግድ ላይ የተሰማሩ አካላት ገልጸዋል።
ያረጁ ተሽከርካሪዎች በአካባቢው እና በሰዎች ላይ  እያደረሱ ያሉትን ተፅዕኖ ለመቀነስም መንግስት በተሽከርካሪዎች ላይ ያስቀመጠው ታሪፍ መቀነስ እንዳለበት ፕሮፌሰር ኮንስታንቲኖስ ተናግረዋል።
ይሁንና፣ የመንግስት ባለስልጣናት ለግል የሚዉሉ ተሽከርካሪዎች እንደቅንጦት የሚታዩና ከቀረጥ የሚገኘው ገንዘብም በአዲስ አበባ ስራ ለጀመረው ቀላል የባቡር አገልግሎቶች አይነት መሰረተ-ልማቶች እንደሚውል መግለጻቸውን CNN በሪፖርቱ አቅርቧል።

No comments:

Post a Comment