Monday, April 11, 2016

የወልቃይት ጠገዴና ፀለምት ተወላጆች በኒዉዚላንድ ኦክላንድ የጠሩት ስብሰባ በተሳካ ሁኔታ ተጠናቋል።


ሚያዚያ ፫( ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በኒዉዚላንድ ኦክላንድ ነዋሪ የሆኑት ኢትዮጵያዉያኖች አጋርነታቸዉንና ወልቃይት አማራ እንጂ ትግሬ አይደለም በሚለዉ የማንነት ጥያቄ ከወልቃይት ጠገዴና ፀለምት ሕዝብ ጋር መሆናቸዉንና ድጋፋቸዉን ለመስጠት ያላቸዉን ቁርጠኝነት ገልጸዋል፡፡
ስብሰባዉንም በእንኳን ደህና መጣችሁ የከፈቱት አቶ አረፈዐይኔ መኮንን በአገር ዉስጥ የወልቃይት ጠገዴና ፀለምት የማንነት ሕዝብ ጥያቄ ሕገመንግስቱ በሚፈቅደዉ መሰረት የማንነታቸዉን ጥያቄ 50 ሺ የሚሆኑ አባወራ አስፈርመዉ ሕጋዊ በሆነ መንገድ አቅርበዉ የተመለሰላቸዉ መልስ ግን እስራት ግርፋት ስደት እንግልት ከዚያም ሲያልፍ ግድያ መሆኑን ነዉ። አሁንም ወጣቱ የሚደርስበት ችግር እቤቱ ለማደር በመቸገሩ ዱር ቤቴ ያለበት መሆኑንም አያይዘዉም ገልፀዋል።
ይህም በመሆኑ እኛ ኢትዮጵያዉያኖች ዛሬ አማራዉ ላይ እየደረሰዉ ያለዉ ጥቃት ከኢትዮጵያ የነፃነት ጥያቄ የተለየ ባለመሆኑ እኛም ይህን የነፃነት ጥያቄ አብረን ከጎን በመቆም ማድረግ የምንችለዉን ሁሉ ማድረግ ይገባናል በማለት ለተሰብሳቢዉ ገለፃ አድረገዋል።
በዚህ የወልቃይት ጠገዴ የማንነት ጥያቄ ላይ በተጠራዉ ስብሰባ አቶ ገ/መድህን አርአያ በስካይፕ በመገኘት በቦታዉ ለተገኘዉ ሕዝብ የወያኔን አስከፊ የሆነ አገር የማጥፋት አጀንዳዉን ገና ጫካ እያለ ሲመሰረት ጀምሮ ይዞት የተነሳ መሆኑን ለተሰብሳቢዉ ገልፀዋል።
በቀጣይም የወልቃይት ተወላጅ የሆኑትም አቶ አበራ በራሳቸዉ እና በቤተሰቦቻቸዉ ሕይወት ወያኔ በወልቃይት ጠገዴ ሕዝብ ላይ በ1972 ዓ.ም ወልቃይት የትግራይ መሬት ነዉ እናንተም ትግሬዎች ናችሁ በማለት ጦርነት በማወጅ በርካታ ያካባቢዉን ሰዎች ገለዉ በተወለዱበት አገር ቤተክርስቲያን እንኳን እንዳይቀበሩ ያደረጉበት እና የነበረዉን ንብረታቸዉን ዘርፈዉ መሔዳቸዉን ተናግረዋል፡፡ አያይዘዉም ከ1976 ዓ.ም እስከ 1978 ድረስ ሽሬ አዉራጃ ዉስጥ በምትገኝ ልዩ ስሟ ዶጋ ዲት በምትባል ትንሽ መንደር ዉስጥ ከ3ሺ በላይ እስረኛ በነበረበት ከመሬት በታች ባለ እስር ቤት ዉስጥ መከራ መቀበላቸዉንም ተናግረዋል።
በዚህ የሁለት አመት የእስር ቆይታቸዉ ከጓደኞቻቸዉ ጋር በሰንሰለት ታስረዉ ከጎናቸዉ አብረዋቸዉ የታሰሩት ሰዎች ሲሞቱ ከ3 እስከ 4 ቀን ድረስ ሬሳዉን ለማዉጣት ባለመፈለግ እና ሆን ብለዉ ከሬሳዉ ጋር ለ3 እና ለ4 ቀናት አብረዉ ታስረዉ እንዲቆዩ እንዳደረጉዋቸው ተናግረዋል።በዚህ ሁሉ የስቃይ ሕይወት ዉስጥ እሳቸዉም እንደ ጓዶቻቸዉም እግዚአብሔር ሞታቸዉን እንዲያቀርብላቸዉ ይለምኑ እነደነበርም ገልፀዋል።
በማያያዝም በእስር ቤት ዉስጥ የደረሰባቸዉን ግፍና በደል ለተሰብሳቢዉ እጅግ ልብ በሚነካ ሁኔታ የገለፁት አቶ አበራ፣ በእስር ቤት ለምርመራ በቀረቡበት ጊዜ በወያኔ ተጋዳይ በሳንጃ ደረታቸዉን ተወግተዉ ላንድ አመት ያህል ያለ ሕክምና መሰቃየታቸዉን እና በእግዚአብሔር ፈቃድ ከዛ መከራ የወጡበት ሁኔታ እንደገጠማቸዉና ወደ ሱዳን እንደተሰደዱ አስረድተዋል፡፡
በዚህ በወልቃይት ጠገዴ የማንነት ጥያቄ ላይ በአዉስትራሊያ ሜልቦርን እና ፐርዝ እንዲሁም በርካታ ኢትዮጵያዉያኖች በተገኙበት የተሳካ ዉይይት እንደተካሔደ አንዱአለም ሀይለማርያም ከኒዉዚላንድ ኦክላንድ ዘግቦአል።

No comments:

Post a Comment