Friday, April 22, 2016

ዛምቢያ 16 ስደተኛ ኢትዮጵያውያንን ማሰሩዋን አስታወቀች

ሚያዚያ ፲፬(አሥራ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች በዝምባብዌ አድርገው ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሄድ ሲሞክሩ መያዛቸውን የአገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል። ስደተኞቹን ያመላልሳሉ ተብለው የተጠረጠሩ 2 ሰዎች መያዛቸውንም ፖሊስ አስታውቋል። ኢትዮጵያውያኑ 30 ሺ ሽልንግ ለፖሊሶች ጉቦ ለመስጠት መሞከራቸውን ሉሳካ ታይምስ ዘግቧል።

የአሁኑ የእስር ዜና የተሰማው በሕገወጥ መንገድ የታንዛኒያን ድንበር አቋርጣችሁ ገብታችኋል ተብለው በታንዛኒያ ፍርድ ቤት የተበየነባቸውን የእስር ጊዜያት ያጠናቀቁ 74 ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በታንዛኒያና ኬንያ ድንበር ተጥለዋል በሚገኙበት ወቅት ነው። የታንዛኒያ መንግስት በገባችሁበት በኬንያ መልሳችሁ ወደ መጣችሁበት ተመለሱ በማለት ሰብዓዊ መብታቸውን በመጣስ ከሕግ ውጪ ስደተኞቹን ከግዛቱ ሲያባርር የኬንያ መንግስት የስደተኞች ጉዳይ በበኩላቸው ስደተኞቹ የእስር ጊዜያቸውን እንደጨረሱ ወደ ትውልድ አገራቸው መላክ ሲገባቸው ወደ ኬንያ መመለሳቸው አግባብ አለመሆኑን በመቃወም ወደ ግዛቴ አይገቡም በማለት ስደተኞቹ ከማከሰኞ እለት ጀምሮ በታቬታ ድንበር ላይ አስታዋሽ አጥተው ለስቃይ መዳረጋቸውን መዘገባችን ይታወቃል። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት መሄጃ ስላጡት ኢትዮጵያውያን እስካሁን ያለው ነገር የለም።

No comments:

Post a Comment