Thursday, July 2, 2015

እስክንድርን ሳስበው…. (አበበ ገላው)

የእስክንድር ትግል እራሱን ጎድቶ ለህዝብ መስዋእት መሆን

ነገ በዲሲ በሚካሄደው ፭ኛው የኢሳት ልደት ላይ ለመገኘት እየበረርኩ ነው። በደመና መሃል እየተጓዙ ምድር ላይ ያሉ ወዳጅ ዘመድን ማሰብ የተለመደ ነገር ይመስለኛል። በአሜሪካን ሰማይ ላይ አሻግሬ ወደ ኢትዮጵያ በአይነ ህሊናዬ ሳማትር አንድ ሰው ጎልቶ እና ገዝፎ ታየኝ። እስክንድር በጨለማ ቤት ተጠፍንገው ከሰው በላይ ገዝፈውና ጎልተው ከታዩኝ ጥቂት ኢትዮጵያዊያን አንዱና ዋነኝው ነው። ። እስክንድር የዘመናችን በላይ ዘለቀ እንደሆነ ምንም ጥርጥር የለውም። መቸም ኢትዮጵያ ለሚሞቱላትና ለሚሰውላት ሁሉ ሲኦል እንደሆነች በታሪክ ተደጋግሞ የታየ ሃቅ ነው።



ገና በልጅነቱ በአሜሪካ ይኖር የነበረው ይህ ታላቅ ሰው ጓዙን ጠቅልሎ ወደ ኢትዮጵያ የተጓዘው ወያኔዎች ኢትዮጵያን ነጻ አወጣን፣ነጻነት ያለገደብ እያሉ በልፈፋ ልብ ሲያማልሉ ነበነበረበት ግዜ ነው።። እስክንድር የወያኔ እርኩስ ባህሪ ጠፍቶት ሳይሆን ያለችዋን ትንሽም ቀዳዳ ልጠቀም ብሎ ኢትዮጵያ የተመለሰው ነግዶ ለማትረፍ፣ ወንም መሬት ቸርቸሮ ለመክበር አልነበረም። በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያ ፈር ቀዳጅ ከነበሩት ጥቂት የግል ፕሬስ ውጤቶች አንዷ የነበረችውን ኢትዮጲስ አቋቁሞ ወያኔን እርቃኑን አስቀረው። ፋሺዝም በትግራይ በሚል በስፋት በተነበበ ጹሁፍ የህወሃቶች የፋሺስት አይዲዎሎጂ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብን ይሁን ለትግራይ ከባድ መከራና ችግር እንደሚያመጣ በመረጃ አስደግፎ ተነተነ። ብዙም ሳይቆይ እርሱና ጋዘጠኛ ተፈራ አስማረ ዘብጥያ ወረዱ። ሃሰተኛው የፕሬስ ነጻነት እወጃ ባዶ መሆኑ ግልጽ ሆነ።

ለወያኔ ጋዜጠኞች ዋነኛ የጥቃት ኢላማ ሆኑ። እስርና ችግር ሳያቆመው ከእር ቤት በወጣ ቁጥር እንደገና ሌላ ጋዜጣ ያሳትማል። ከእኔ ጋር የተገናኘነው ሃበሻ የተባለች የእንግሊዝኛ ጋዜጣ ሲያሳትም ነበር። ለትንሽ ግዜ ቢሆንም አብረን ሰርተናል። ታዲያ ከሚገርመኝ ነገር አንዱ የነረው እስክንድር ከራሱ በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ መብት መጣስ፣ የነጻነት እጦት፣ መዋከብ፣ መታሰር፣ ለሰቆቃና ለሞት መዳረግ እጅግ ያሳስበው ነበር። ሲሰራ ከልቡ ነው። ሲጽፍ ውሎ ሲጽፍ ያድር ነበር። ብዙ ግዜ እዛው ሲለሚነጋበት ቢሮው ፍራሽ አንጥፎ መሬት ላይ ነበር የሚተኛው።

የእስክንድር ትግል እራሱን ጎድቶ ለህዝብ መስዋእት መሆን ነበር። ኢትዮጵያን ጥዬ ለመኮብለል ሳስብ አማከርኩት። ፍጹም አትሂድ ብሎ መከረኝ። እዚሁ ሆነን እንታገል፣ አገራችንን ለወያኔ ጥለን መሄድ ፈጽሞ አይገባም አለ። እኔ ግን ሞቼ እገኛለሁ ብዬ በአቋሜ ጸናሁ።ኢትዮጵያ ውስጥ ተጨቁኖ በስጋት መኖር መሮኛል፣ በፍጹም አልቀርም አልኩት። ከልቡ አዘነ።

የዛሬ 16 አመት አገር ጥዬ በረርኩ። እስክንድር ሲታሰር፣ ሲፈታ፣ ሲታሰር ሲፈታ፣ ለመቁጠር አዳጋች ነበር። ከሁሉ በላይ ያዘንኩት ከእራሱ አልፎ ከነመላ ቤተሰቡ ቃሊቲ መውረዱ ነበር። ባለቤቱ ሰርካለም አብራው ስትታሰር ልጃቸው ናፍቆት ገና ጽንስ ነበር። ጨካኞቹ ወያኔዎች ጥላቻቸው ከአባቱ አልፎ ለጽንሱ ተረፈው። የሰርካለም ምጥ ከባድ ነበር። እግር ተወርች ታስሮ ምጥ መያዝን ያህል የከፋ ምን ነገር ይኖራል።

አሁንም እስክንድር እንደታሰረ ነው። ቢያንስ ባለቤቱ ሰርካለም እና ልጁ ናፍቆት ከኛው መሃል ይኖራሉ። ሌላ ማድረግ ባንችል የዚህን ታላቅ ኢትዮጵያዊ ቤተሰብ በሚቻለን ሁሉ መደገፍ ብቸኝነት እንዳይሰማቸው መጠየቅ የኛ ድርሻ ነው። ናፍቆት የጀግኖች ልጅ ብቻ አይደለም። በእስር ቤት ተወልዶ መከራን ተቋቆሞ ከሞት የተሳ ልጅ ነው። ልጁም እንደወላጆቹ የራሱ ታሪክ አለው።

እስክንድርን ሳስበው ይገርመኛል። ሚሊዮኖች ቢያንቀላፍም ፈጽሞ የማይተኛ ሰው። ለዘጠናኛ ግዜ ታስሮ አስረኛው ዙር ዙር ቢመጣ የማይበገር ሰው። አትጠራጠሩ እስክንድር ከጥቂቶቹ ኢትዮጵያዊያን ማንዴሎች አንዱ ነው። እነሱን አሳስረን እኛ ማንቀላፋት ይቻለናል ወይ


No comments:

Post a Comment