Wednesday, July 1, 2015

እነ ወይንሸት ሞላ እያንዳንዳቸው 5000 ብር ዋስ ተጠየቀባቸው

እነ ወይንሸት ሞላ እያንዳንዳቸው 5000 ብር ዋስ ተጠየቀባቸው
•ነገ ደግሞ ይግባኝ በተባለባቸው ጉዳይ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ
በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር
መንግስት አይ.ኤስ.አይ.ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ የታሰሩት ወንይሸት ሞላ፣ ኤርሚያስ ፀጋዬ፣ ዳንኤል ተስፋዬና ቤተልሄም አካለ ወርቅ ፖሊስ ምስክሮችን አስፈራርተውብኛል ካለው ጉዳይ ጋር በተያያዘ ዛሬ ሰኔ 23/2007 ዓ.ም በቄራ ፍርድ ቤት ቀርበው እያንዳንዳቸው የ5000 ብር ዋስ ተጠይቆባቸዋል፡፡
በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የስድስተኛ ፖሊስ ጣቢያ እነ ወይንሸት ቀደም ብሎ ጉባኤንና ስብሰባን በማወክ በተከሰሱበት ወቅት ምስክሮቼን አስፈራርተውብኛል ያለው ፖሊስ ለምስክርነት የማረሚያ ቤት ፖሊስን ቢያስመዘግብም በዛሬው ዕለት ምስክሮቹን ይዞ መቅረብ ሳይችል ቀርቷል፡፡ በዚህም ተጨማሪ ቀጠሮ ጠይቆ የነበር ቢሆንም፣ እነ ወይንሸት የዋስትና መብታቸው እንዲከበርላቸው ጠይቀው እያንዳንዳቸው 5000 ብር ዋስ እንዲያስይዙ ፍርድ ቤቱ አዝዟል፡፡
እነ ወይንሸት ሞላ ቀደም ሲል የቄራ ፍርድ ቤት ከእስር እንዲወጡ ውሳኔ በሰጠበት ጉዳይ ላይ የስድስተኛ ፖሊስ ይግባኝ ስለጠየቀባቸው በሚል ነገ ሰኔ 24/2007 ዓ.ም ቂሊንጦ እስር ቤት የሚገኘው ማስተዋል ፍቃዱን ጨምሮ ልደታ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ እነ ወይንሸት በፍርድ ቤት ከእስር እንዲፈቱ ቢወሰንላቸውም ፖሊስ ውሳኔውን ባለማክበር አስሯቸው እንደሚገኝ ተመልክቷል፡፡
መንግስት ሚያዝያ 14/2007 ዓ.ም ከጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ጋር በተያያዘ ብዙ ዜጎችን አስሮ እንደሚገኝ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡


No comments:

Post a Comment