Friday, July 3, 2015

ሜሮን አለማየሁ 6 ወር ተፈረደባት

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

መንግስት አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም በጠራው ሰልፍ ሰበብ ታስራ ‹‹ሰላማዊ ሰልፍና ስብሰባ በማወክ›› የተከሰሰችው ሜሮን አለማየሁ የ6 ወር እስር ተፈረደባት፡፡ ሜሮን አለማየሁ ሚያዝያ 14 በተጠራው ሰልፍ ላይ ‹‹ወያኔ ሌባ፣ መንግስት የለም፣ አትነሳም ወይ፣ የታረደው ወገን ያነተ አይደለም ወይ›› በሚል ሁከትና ብጥብጥ ፈጥራለች ተብላ በተከሰሰችበት በዋስ ወጥታ ጉዳዩን ስትከታተል የቆየች ሲሆን ዛሬ ሰኔ 26/2007 ዓ.ም በጎፋ ፍርድ ቤት ቀርባ 6 ወር ተፈርዶባታል፡፡




አቃቤ ህግ በክሱ ሜሮን አለማየሁ ድንጋይ እንደወረወረች ቢጠቅስም፣ የአቃቤ ህግ ምስክሮች ስትወረውር አላየንም ብለው፡፡ በተጨማሪም አቃቤ ህግ ሜሮን ከ200-300 የሚሆኑ ሰዎችን በመምራት ሁከትና ብጥብጥ እንደፈጠረች ጭብጥ ቢያስይዝም ምስክሮቹ አቃቤ ህግ እንዳለው ሳይሆን ሜሮን አለማየሁን ከ20-30 ከሚሆኑ ሰዎች ጋር እንዳዩዋት መስክረዋል፡፡ በተመሳሳይ አቃቤ ህግ ሜሮን አለማየሁ ብጥብጡን የፈጠረችው መስቀል አደባባይ ላይ ነው ሲል ምስክሮቹ አቃቤ ህግ ባለው ሰዓት ከጎተራ ወደ መስቀል አደባባይ በሚወስደው መንገድ እንዳዩዋት መስክረዋል፡፡

አቃቤ ህግ ሜሮን አለማየሁ ብጥብጡን የፈጠረችው ከ3 ሰዓት እስከ 4 ሰዓት ባለው ጊዜ ነው ያለ ሲሆን የሜሮን አለማየሁ የመከላከያ ምስክሮች ከ3፡20 እስከ 5 ሰዓት ከእሷ ጋር አምባሳደር አካባቢ እንደነበሩ አስረድተዋል፡፡ ሆኖም ፍርድ ቤቱ ምስክሮቹ ከ3፡20 በፊት የት እንደነበረች አላስረዱም እንዲሁም ካፌ ውስጥ የጠጡትን ለስላሳ አልገለጹም በሚል ምስክርነቱን ውድቅ አድርጌዋለሁ ብሏል፡፡


No comments:

Post a Comment